የክላርኔት የሙዚቃ መሣሪያ ተጫዋቹ ዳዊት ፍሬው አስከሬን ነገ አዲስ አበባ ይገባል
አዲስ አበባ፣ ግንቦት 4፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የክላርኔት የሙዚቃ መሣሪያ ተጫዋቹ ዳዊት ፍሬው አስከሬን በነገው ዕለት ከጣሊያን አዲስ አበባ እንደሚገባ ተገልጿል፡፡
ከሙያ አጋሮቹ የተውጣጣው አስተባባሪ ኮሚቴ ዛሬ በሰጠው መግለጫ÷ የዳዊት ፍሬው አስከሬን ከጣሊያን ዛሬ ዕኩለ ለሊት ላይ ተነስቶ ነገ ማለዳ 12 ሰዓት ላይ አዲስ አበባ እንደሚገባ አስታውቋል።
የዳዊት ፍሬው አስከሬን በቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ነገ 3 ሰዓት ላይ አቀባበል ከተደረገለት በኋላም ወደ ወላጅ እናቱ ቤት እንደሚገባ ተገልጿል።
እሑድ ጠዋት በሀገር ፍቅር ቴአትር ለሙያው ባበረከተው አስተዋጽኦ በሚመጥን መልኩ የክብር ሽኝትና የሻማ ማብራት ስነ-ስርዓት እንደሚከናወንም ተጠቁሟል፡፡
የቀብር ስነ-ስርዓቱም የፊታችን እሑድ 6 ሰዓት ላይ በቅድስት ስላሴ ካቴደራል እንደሚፈፀም ነው ኮሚቴው ያስታወቀው፡፡
በቅድስታ አባተ