Fana: At a Speed of Life!

በምሥራቅ አፍሪካ ተጎጂዎችን ለመደገፍ የሚውል 2 ነጥብ 4 ቢሊየን ዶላር መገኘቱ ተነገረ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 17፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በምሥራቅ አፍሪካ የሚያደርገውን እርዳታ ለመደገፍ የሚውል 2 ነጥብ 4 ቢሊየን ዶላር አገኘ።

የተገኘው ገንዘብ ድርጅቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ በኬንያ እና ሶማሊያ ለሚገኙ ወደ 32 ሚሊየን የሚጠጉ ዜጎች ድጋፍ ለማድረግ የሚውል መሆኑ ታውቋል።

ድጋፉ የተመድ አጋር ከሆኑ ማኅበረሰቦች ፣ ሰብዓዊ ድርጅቶች ፣ ባለሥልጣናት እና ለጋሾች መገኘቱን የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ ድጋፍ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ) መረጃ ያመላክታል፡፡

ዛሬ ቃል የተገባውን የገንዘብ ድጋፍ ማግኘት የተቻለው በኒውዮርክ በተዘጋጀ ከፍተኛ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ-ግብር ላይ ሲሆን ተመድ በምስራቅ አፍሪካ በሰው ሰራሽና በተፈጥሮ አደጋዎች ሳቢያ ችግር ላይ የሚገኙ ዜጎችን ለመርዳት 7 ቢሊየን ዶላር እንደሚያስፈልገው ገልጾ ነበር፡፡

መርሐ-ግብሩን ተመድ ፣ ጣሊያን፣ ኳታር ፣ እንግሊዝ እና አሜሪካ ከኢትዮጵያ ፣ ኬንያ እና ሶማሊያ መንግስታት ጋር በመተባበር አዘጋጅተውታል፡፡

አሜሪካ፣ የአውሮፓ ኮሚሽን፣ ብሪታንያ፣ ጀርመን እና ኔዘርላንድስ አብዛኛውን ገንዘብ ለመስጠት ቃል የገቡ ሀገራት ናቸው።

በቀጣናው ባለፉት 5 የዝናብ ወቅቶች በቂ ዝናብ ባለመዝነቡ በተከሰተው ድርቅ፣ በግጭት ለተጎዱ እንዲሁም የሀገራቱ ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ የተረጋጋ ባለመሆኑ ድጋፉ ማስፈለጉም ነው የተገለጸው፡፡

የተገኘው ድጋፍ ተጎጂዎችን በጊዜያዊነት ለመደገፍ እንጂ ችግሩን በዘላቂነት የሚፈታ እንዳልሆነ ተጠቁሟል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.