ምርትና ምርታማነትን የሚጨምሩ ሥራዎች በመሥራት ፈተናን መሻገር እንደሚቻል ተመላከተ
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 9 ፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ፈጠራን እንዲሁም ምርትና ምርታማነትን የሚጨምሩ ሥራዎችን በትኩረት በመሥራት የሚፈታተኑ ጉዳዮችን መሻገር እንደሚቻል የብልፅግና ፓርቲ ሥራ አሥፈፃሚና የደቡብ ምዕራብ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ-መስተዳድር ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ገለጹ።
ለአምሥት ቀናት በጅግጅጋ ከተማ ሲካሄድ የቆየው የሶማሌ ክልል የከፍተኛና መካከለኛ አመራርሮች ሥልጠና ዛሬ ተጠናቋል።
የደቡብ ምዕራብ ሕዝቦች ክልል ርዕሰ መስተዳድርና የብልጽግና ፓርቲ ሥራ አሥፈጻሚ ነጋሽ ዋጌሾ(ዶ/ር) ÷ ለአምሥት ቀናት ሲካሄድ የቆየው መድረክ በፓርቲው ሥራ አሥፈጻሚና ማዕከላዊ ኮሚቴ በተቀመጡ አቅጣጫዎች ላይ በየደረጃው ከሚገኙ አመራሮች ጋር ግልጽነት የተፈጠረበት ነውም ብለዋል።
በተጨማሪም ÷ የተዛቡና የተሳሳቱ ቡድናዊ ፍላጎት የሚያንፀባርቁ መረጃዎችን በወቅቱ ህዝቡ ትክክለኛ መረጃ እንዲያገኝ በማስቻል የውል እውነቶችን ማፅናት እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
በመድረኩ ከተሳተፉ አመራሮች መካከል ወይዘሮ ሄቦ አሕመድ ÷ሥልጠናው የፓርቲ የውስጥ ነፃነትን በማረጋገጥ መንግስታዊ አገልግሎቶች የሕዝቡን ጥያቄዎች መመለስ በሚያስችሉ መልኩ ስለመመራታቸው በቂ ግንዛቤ ማገኘታቸውን ተናግረዋል።
አቶ የሱፍ መሐመድም ÷ በተቀመጠው አቅጣጫ መሠረት በሕዝቡ ዘንድ የሚታዩ የኑሮ ውድነት ለመፍታት ፣ በልማት፣ በሠላምና በሌሎች ጉዳዮች ፍጥነትንና ፈጠራን ባማከለ ሁኔታ እንዲፈፀም የሚረዳን ነው ማለታቸውን ከፓርቲው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡