ሕገ ወጥ ምንዛሬ ሲፈፅም ነበር የተባለ ግለሰብ ከተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች ጋር በቁጥጥር ስር ዋለ
አዲስ አበባ፣ሰኔ 18፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲስ አበባ ከተማ ቦሌ ክፍለ ከተማ ሕገ ወጥ የገንዘብ ምንዛሬ ሲፈፅም ነበር የተባለ ግለሰብ ከተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች ጋር በቁጥጥር ስር ዋለ፡፡
በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 ልዩ ቦታው ጎላጉል አውራሪስ ሆቴል ጀርባ አካባቢ በተደረገ ክትትልና ፍተሻ ነው ከአንድ ተጠርጣሪ መኖሪያ ቤት ውስጥ የተለያዩ ሀገራት ገንዘቦች የተያዙት።
ፖሊስ የፍርድ ቤት የመበርበሪያ ትዕዛዝ አውጥቶ ባደረገው ፍተሻ 8 ሺህ 342 የአሜሪካን ዶላር፣ 1 ሺህ 872 የሳዑዲ ሪያል፣ 1 ሺህ 735 ድርሃም እንዲሁም የስዊዲን፣የሱዳን፣የታይዋን፣የቱርክና የኳታር ገንዘቦች ተይዘዋል፡፡
ለዚሁ ስራ የሚያገለግል 525 ሺህ የኢትዮጵያ ጥሬ ብር የተገኘ ሲሆን÷በወንጀል ድርጊቱ የተጠረጠረ አንድ ግለሰብ በሕግ ቁጥጥር ስር መዋሉንም የፖሊስ መረጃ ያመላክታል፡፡