ኢትዮጵያ እና ቻይና በታዳሽ ኃይል ልማት ላይ በጥምረት የሚያከናውኑትሥራ ተደነቀ
አዲስ አበባ፣ ሰኔ 25፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ እና ቻይና በታዳሽ ኃይል ልማት ላይ በጥምረት እያከናወኑ የሚገኘውን ሥራ የተመድ የልማት ፕሮግራም (ዩ ኤን ዲፒ) አደነቀ፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም÷ በ “ግሎባል ደቡብ” መርሐ-ግብር በተመጣጣኝ ዋጋ ታዳሽ ኃይልን ለማስተዋወቅ ከቻይና ጋር የመሠረትኩት አጋርነት ይበል የሚያሠኝ ነውም ብሏል፡፡
ድርጅቱ በኢትዮጵያ የተጀመረውን የታዳሽ ኃይል ተደራሽነትን የማሥፋት መርሐ-ግብር ወደ አፍሪካ ሀገራት ማሥፋት እንደሚገባ ገልጿል፡፡
የተመድ የልማት ፕሮግራም በኢትዮጵያ ምክትል ተወካይ ክሊፋስ ቶሮሪ ÷ በቻይና እና በኢትዮጵያ መካከል በዘላቂ የኃይል አጠቃቀም ላይ እየተሠሩ ያሉ ሥራዎች ይደነቃሉ ማለታቸውን ሲ ጂ ቲ ኤን ዘግቧል፡፡
የታዳሽ ኃይል ቴክኖሎጂን ከማስተዋወቅ አንጻርም ባዮጋዝ እና ከፀሐይ የሚገኝ ኃይልን ማስተዋወቅ እና በሥፋት መጠቀም ወሳኝ ስለመሆኑ አስገንዝበዋል፡፡
ኢትዮጵያ ከቻይና ጋር በመተባበ ግብርና-መር ኢንዱስትሪውን በመጠቀም ታዳሽ ኃይል ላይ እያከናወነች ያለውን ሥራም አወድሰዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የደቡብ – ደቡብ ትብብርን ለመደገፍ፣ ከኢትዮጵያ እና ቻይና ጋር በሦስትዮሽ የትብብር ማዕቀፍ በጋራ ለመሥራት ቁርጠኛ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡