Fana: At a Speed of Life!

የተማሪዎች ምደባ ዩኒቨርሲቲዎች ያላቸውን የቅበላ አቅም ታሳቢ ያደረገ ነው – ትምህርት ሚኒስቴር

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 21፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ምደባ በተማሪዎች የተመረጡ ዩኒቨርሲቲዎች ያላቸውን የቅበላ አቅም ታሳቢ ያደረገ መሆኑን የትምህርት ሚኒስቴር ገለጸ፡፡
በ2015 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሄራዊ ፈተና ወስደው ያለፉ ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ ምደባ አሰራርን አስመልክቶ ሚኒስቴሩ ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡
የማብራሪያው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ቀርቧል፡-
የዩኒቨርስቲ ምደባ
በ2015 ዓ.ም የ12ኛ ክፍል መልቀቂያ ብሄራዊ ፈተና ወስደው ያለፉ ተማሪዎች የዩኒቨርሲቲ ምደባ አሰራርን አስመልክቶ የተሰጠ ማብራሪያ
የተማሪ ምደባ መስፈርቶች፡-
1. 1000 ለሚሆኑ ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ተማሪዎች፡- የምደባ ስርዓቱ በተፈጥሮም ሆነ በማህበራዊ ሳይንስ መስኮች 1000 ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገቡ ተማሪዎችን በመጀመሪያ የዩኒቨርስቲ እና የትምህርት መስክ ምርጫቸው ምደባ የሚካሄድ ይሆናል።
2. ውጤት፡- የምደባ ስርዓቱ እያንዳንዱ ተማሪ ያስመዘገበውን አጠቃላይ ውጤት በምደባ ስርዓት ሂደት ውስጥ መለያ አድርጎ ይጠቀማል፡፡የተሻለ ውጤት ያስመዘገቡ ተማሪዎች ሌሎች ተፈጻሚ የሚሆኑ ህግና ደንቦችን ባልጣሰ መልኩ ምርጫቸውን በመጠበቅ ረገድ ቅድሚያ ይሰጣቸዋል፡፡
3. የዩኒቨርሲቲ ምርጫ፡- የምደባ ስርዓቱ በተማሪዎች የተመረጡ ዩኒቨርሲቲዎች ያላቸውን የቅበላ አቅም ታሳቢ ያደረገ ነው፡፡ ተማሪዎች 46 ዩኒቨርሲቲዎች ለምርጫ ቀርበውላቸዋል፡፡ መረጃው የተሰበሰበው https://portal.etherenet.edu.et ላይ ነው፡፡
4. በተማሪዎች የተመረጡ ተቋማት ያላቸው የትምህርት ፕሮግራሞች ፡- የምደባ ስርዓቱ በተማሪዎች የተመረጡ የትምህርት ፕሮግራሞች እና የተመረጡት ዩኒቨርሲቲዎች ያላቸውን የትምህርት ፕሮግራም መሰረት ያደረገ እንዲሆን ተደርጓል፡፡
5. ጾታ ፡- በተቋማት የጾታ ተዋጽኦን ለመጠበቅ በሚኖረው የምደባ ስርዓት የጾታ ተዋጽኦና ሚዛን እንዲጠበቅ ተደርጓል፡፡
6. የትምህርት ቤት ተዋጽኦ ፡- የምደባ ስርዓቱ ከተለያዩ ትምህርት ቤቶች የሚመደቡ ተማሪዎችን ተዋጽኦ በጠበቀ መልኩ እንዲሆን ያግዛል፡፡
ይህም ከአንድ ት/ቤት የወጡ ተማሪዎች በአንድ ዩኒቨርሲቲ ወይም ፕሮግራም ውስጥ እንዳይታጨቁ ይደርጋል፡፡
7. የውጤት ተዋጽኦ ፡-የምደባ ስርዓቱ ተማሪዎች ያስመዘገቡትን ውጤት ታሳቢ ያረገ ሲሆን ይህም ተመሳሳይ ውጤት ያስመዘገቡ ተማሪዎች አንድ ላይ እንዳይመደቡ በማድረግ የተለያየ ችሎታና ተሰጥኦ ያላቸው ተማሪዎችን ቀላቅሎ ለማስተማር ያግዛል፡፡
8. ወሊድን በተመለከተ፡- የምደባ ስርዓቱ እንደ ወሊድ ያሉ ልዩ ሁኔታዎችን ያማከለ ነው፡፡ በመሆኑም በመሰል ሁኔታ ውስጥ ያሉ ተማሪዎች በተመደቡበት ዩኒቨርሲቲ ለመቀጠል የሚቸገሩ ከሆነ ትክክለኛ ለውጥና ድጋፍ የሚደረግ ይሆናል፡፡ መረጃዎቹ የተሰበሰቡት https//student.ethernet.edu.et ላይ ነው፡፡
•አስፈላጊ ማስረጃዎች: – ከትምህርት ቤታቸው የድጋፍ ደብዳቤ እና የህጻናት የክትባት ካርድ
9. ትክክለኛ የሕክምና ቦርድ ማስረጃዎች፡- በምደባ ወቅት የጤና ችግር ኖሮባቸው ትክክለኛ የሕክምና ማስረጃ ላላቸው ተማሪዎች ምደባው በተለየ መልኩ ሊታይ ይችላል፡፡
• አስፈላጊ ማስረጃዎች፡ ከትምህርት ቤታቸው የድጋፍ ደብዳቤ እና ከህዝብ ጤና ተቋማት የህክምና ምስክር ወረቀት በሶስት ዶክተሮች እና በህክምና ዳይሬክተሩ የጸደቀ።
• የዚህ አይነት መረጃ የተሰበሰበው https://student.ethernet.edu.et በመጠቀም ነው።
10. ተመሳሳይ ጾታ ያላቸው መንትዮች (identical twins) ፡- በተማሪዎቹ መካከል ተመሳሳይ ጾታ ያላቸው መንትዮች ካሉ የምደባ ስርዓቱ ከፍተኛ ነጥብ ያገኘው/ችው ተማሪ ከተመደበበት/ችበት የትምህርት ተቋም ቀሪው መንትያ ደግሞ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በቀጥታ ይመድባል። የዚህ አይነት መረጃ የተሰበሰበው https://student.ethernet.edu.et ላይ ነው።
• አስፈላጊ ማስረጃዎች፡- ከትምህርት ቤታቸው የድጋፍ ደብዳቤ እና የልደት የምስክር ወረቀት፣
11. የአካል ጉዳት ያለባቸው ተማሪዎች:- የምደባ ሲስተሙ የአካል ችግር ላለባቸው ተማሪዎች እኩል እድሎችን የሚሰጥ ሲሆን ልዩ ፍላጎቶቻቸውን እና ለምደባ መስፈርቶቻቸውን ግምትውስጥ በማስገባት የሚሰራ ይሆናል። የዚህ አይነት መረጃ የተሰበሰበው https://student.ethernet.edu.et በመጠቀም ነው።
• አስፈላጊ ማስረጃዎች፡ ከትምህርት ቤታቸው የድጋፍ ደብዳቤ እና የአካል ችግር ያለበትን የሰውነት ክፍል የሚያሳይ ፎቶግራፍ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፣
ማሳሰቢያ፣ ሀሰተኛ የሕክምና ማስረጃ የሚያቀርብ ተማሪ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ከምደባ ውጭ የሚሆን መሆኑን እንገልጻለን፡፡
የኢፌዲሪ ትምህርት ሚኒስቴር!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.