Fana: At a Speed of Life!

ሰን አውቶና ካርበን ባንክ በኢትዮጵያ በልዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ለመሰማራት ፍላጎት እንዳለው ገለፀ

 

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 30፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ሰን አውቶና ካርበን ባንክ በኢትዮጵያ በልዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ለመሰማራት ፍላጎት እንዳለው ገለፀ፡፡

በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች የኢትዮጵያ አምባሳደር ዑመር ሁሴን ከሰን አውቶና ካርበን ባንክ ማኔጀር አብዱል ጋሃኒ (ዶ/ር) ጋር በኢንቨስትመንትና በአረንጓዴ አሻራ ዙሪያ ተወያይተዋል።

በውይይታቸውም አብዱል ጋሃኒ(ዶ/ር)÷ በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) አነሳሽነት በኢትዮጵያ የተጀመረው አረንጓዴ አሻራ ያመጣውን ውጤት አድንቀዋል፡፡

ድርጅታቸውና እህት ኩባንያዎቹ ወደ ኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ለማስመጣት እንዲሁም ከአሁን በፊት ያልታዩ ልዩ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ ለመሰማራት ፍላጎት እንዳላቸው ገልጸዋል።

ይህንኑ ለማሳካትም ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠይቀዋል፡፡

አምባሳደር ዑመር ሁሴን በበኩላቸው÷ ድርጅታቸውና እህት ኩባንያዎቹ ኢትዮጵያ ውስጥ በኢንቨስትመንት መሰማራት እንዲችሉ በትብብር እንደሚሰራ መግለፃቸውን ከአቡዳቢ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

በቀጣይም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር ኩባንያው ወደ ኢትዮጵያ የቅድመ ኢንቨስትመንት ጉዞ እንዲያደርግና በዘርፎቹ ለመሰማራት የሚችልበትን መንገድ ለማመቻቸት ጥረትና ክትትል እንደሚደረግም ተናግረዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.