Fana: At a Speed of Life!

የቫይታሚን ዲ እጥረት ስለሚያስከትለው የጤና ዕክል ምን ያህል ያውቃሉ?

አዲስ አበባ፣ ጥር 1፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ማንኛውም የሕብረተሰብ ክፍል ማለትም (ሕጻናት፣ ወጣቶች፣ አዛውንቶች) በቫይታሚን ዲ እጥረት ሊጠቁ እንደሚችሉ ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡

በአብዛኛው የከተማ ነዋሪዎች ፀሐይ የመሞቅ ልምዳቸው ዝቅተኛ ስለሆነ ለቪታሚን ዲ እጥረት የመጋለጥ ዕድላቸው ከፍተኛ መሆኑንም ይጠቁማሉ፡፡

የቫይታሚን ዲ እጥረት ከሚያስከትላቸው የጤና ችግሮች መካከል÷ የወገብ ህመም፣ የነርቭ ህመም፣ የጡንቻ መዛልና መልፈስፈስ፣ የአንጎልና አዕምሮ ህመም (አልዛይመር፣ መልቲፕል እስክለሮሲስ እና ድባቴ) እንደሚገኙበት ይናገራሉ፡፡

በዋናነት ከፀሐይ ብርሃን እንዲሁም ከምግብ የሚገኘው ቪታሚን ዲ÷ ለአጥንት መጠንከር ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንዳለውም ነው ባለሙያዎች የሚናገሩት፡፡

በቂ የፀሐይ ብርሃን በማግኘት አጥንትን ከመሰበር እና ከመሳሳት መከላከል የሚቻል ሲሆን÷ በተፈጥሮ የፀሐይ ብርሃን ለማያገኙ ሰዎች በምግብ አሊያም በመድሐኒት እንዲያገኙ ይደረጋል ይላሉ።

የቪታሚን ዲ እጥረት ሲኖር የነርቭ ኅዋሳት ሥራ ይስተጓጎላል፤ የነርቭ ኅዋሳት ለሚከውኑት ሥራ የሚያስፈልጋቸው ሆርሞኖች እንዲመረቱ ቪታሚን ዲ ትልቅ ድርሻ አለው ይላሉ ባለሙያዎቹ ሲያብራሩ፡፡ እነዚህ ሆርሞኖች ደግሞ ሰው እንዲደሰት ብሎም ጤናማ እሳቤ እንዲያመነጭ ይረዳሉ ነው የሚሉት፡፡

የቫይታሚን ዲ እጥረት የሐሳብ መጋጨትን ያስከትላል፤ በዚህም ሰዎች ወደ ድባቴና የተዛባ አዕምሯዊ መዋቅር ሊሸጋገሩ ይችላሉ፡፡

ጸሐይ በመሞቅ በቂ ቫይታሚን ዲ ማግኘትትና በቪታሚን ዲ እጥረት የሚከሰቱ የጤና ዕክሎችን መከላከል እንደሚገባም ይመክራሉ፡፡

ፀሐይ በውስጡ ጠቃሚ እና ጎጂ ጨረራዎችን ስለያዘ ሲበዛ ለቆዳ ካንሰር ያጋልጣል የሚሉት ባለሙያዎቹ÷ ይህን ለመከላከልም የቀትር ፀሐይን አለመጠቀም ተመራጭ ነው ይላሉ።

በተጨማሪም ቪታሚን ዲ÷ የጡንቻ ጤንነትን በመጠበቅ፣ የጀርባ አጥንትን በማጠንከር ፣ የበሽታ መከላከያ ሥርዓትን አደራጅቶ ከህመም በመታደግ፣ የሥነ- አዕምሮ ጤናን በማስተካከል ረገድ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ይጠቅሳሉ፡፡

ቪታሚን ዲን ለማግኘትም÷ የጠዋት አልያም የማታ ፀሐይን ያለልብስና ያለቅባት ቢያንስ ለግማሽ ሰዓት በሳምንት ለአራት ቀናት መሞቅ ይመከራል መባሉን ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.