Fana: At a Speed of Life!

ዓድዋን ስናከብር ከአባቶቻችንን ትምህርት ወስደን አዲስ ታሪክ መጻፍ እንደምንችል በመገንዘብ ሊሆን ይገባል – አቶ ጥላሁን ከበደ  ጥላሁን ከበደ

አዲስ አበባ፣ የካቲት 22፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የዓድዋ ድል በዓልን ስናከብር ከአባት እናቶቻችንን ትምህርት ወስደን አዲስ ታሪክ መጻፍ እንደምንችል በመገንዘብ ጭምር ሊሆን ይገባል ሲሉ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ጥላሁን ከበደ ገለፁ።

ርዕሰ መስተዳድሩ ለ128ኛው የዓድዋ ድል በዓል የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል።

በመልዕክታቸው፤ የዓድዋ ድል በዘመን የማይደበዝዝ ዘላለማዊ ክብር እና ኩራት ያጎናጸፈን የሸናፊነት የጋራ አኩሪ ታሪካችን ነው ብለዋል።

ድሉ መላ ኢትዮጵያውያንን ከዳር እስከ ዳር በላቀ የሀገር ስሜት፤ ወኔ እና ጀግንነት በማሰባሰብ በተባበረ ኅብረ ብሔራዊ አንድነት የወራሪ ኃይል ጀግኖች አባቶቻችንና እናቶቻችን ድል ያደረጉበት በዘመን የማይደበዝዝ ዘላለማዊ ክብር እና ኩራት ያጎናጸፈን የሸናፊነት የጋራ አኩሪ ታሪካችን ነው ሲሉ ገልጸዋል፡፡

ድሉ ከኢትዮጵያውያን አልፎ ለመላው ጥቁር ሕዝቦች የነፃነት ጎህን የቀደደ ነው ሲሉም ገልፀዋል።

የዓድዋ ድልን ስናከበር በድሉ እየኮራን የማይቻል ከሚመስለው የአባት የእናቶቻችን የአንድነትና የአልሸነፍ ባይነት የተጋድሎ ታሪክ ትምህርት በመውሰድ በአንድ ልብ ከተነሳን ድህነትን ድል ነስተን ብልጽግናችንን በማረጋገጥ ዳግም አዲስ ታሪክ ከመጻፍ የሚያግደን ምንም ኃይል አለመኖሩን በመገንዘብ ጭምር ሊሆን ይገባል ሲሉም አሳስበዋል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.