Fana: At a Speed of Life!

በአዲስ አበባ “ምግባችንን ከጓሯችን” የተሰኘው የ2012 የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት መርኃ ግብር ተጀመረ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 1 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) በአዲስ አበባ “ምግባችንን ከጓሯችን” የተሰኘው የ2012 የክረምት በጎ ፍቃድ አገልግሎት መርኃ ግብር በዛሬው ዕለት በይፋ ተጀመረ።

መርኃግብሩን የአዲስ አበባ ከተማ ምክትል ከንቲባ ኢንጂነር ታከለ ኡማ እና የግብርና ሚኒስትር ዑመር ሁሴን አስጀምረዋል።

በበጎ ፍቃደኛ የአዲስ አበባ ወጣቶች የችግኝ ተከላ እና የአካባቢው አርሶ አደሮችን ማሳ የማረስ የክረምት በጎ ፍቃድ ማስጀመሪያ መርኃ ግብር አቃቂ ክፍለ ከተማ ወረዳ 11 መንደር 6 ገላኒይዶሮ በተባለው አካባቢ ተካሂዷል።

ከዚህ በኋላ ለቀጣይ አራት ወራት የከተማዋ አርሶ አደሮችን ማሳ በበጎ ፍቃደኛ ወጣቶች የማሳረስ እና በክረምት ችግኝ የመትከል ዕቅድን ለማሳካት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ያዘጋጀው ይህ መርኃ ግብር በተለያየ የበጎ ፍቃድ ዘርፍ ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል ተብሏል።

ምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ አባቶቻችን እኛኑ ለመመገብ ነውና የሚያርሱት፤ የአባቶቻችሁን መሬት ልታርሱ ልታለሰልሱ የመጣችሁ ወጣቶችም ከእነርሱ ምርቃት ተርፎ ምስጋናም ይገባችኋል ብለዋል።
 
ይህን አርአያ ሌሎች ወጣቶችም እንዲከተሉ ጥሪ አቅርበዋል።
 
የግብርና ሚኒስትር ዑመር ሁሴንም ከስራው በላይ የሃሳቡ ጥቅም እንደሚጎላ ገልፀዋል።
 
የከተማ ወጣቶች ከአርሶ አደሩ ጎን መሆናቸውን ማወቅ በራሱ ዋጋው ብዙ ነው ያሉት ሚኒስትሩ በሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ስም ይህ በጎፍቃደኝነት እንዲቀጥል አሳስበዋል።
 
በተጨማሪም ለአርሶ አደር ተወካዮች የከተማ አስተዳደሩ 10 ሚሊየን ብር የሚገመት የማበረታቻና ማዳበሪያና የምርጥ ዘር ስጦታ ሰጥቷል።
 
ለምክትል ከንቲባ ታከለ ኡማ፣ ለግብርና ሚኒስትሩ እና ለሌሎቹም ኃላፊዎች የፈረስና የጋቢ ስጦታ አርሶ አደሮች ሰጥተዋል።
 
በተመሳሳይ በዛሬው እለት በቦሌ ክፍለ ከተማ ወረዳ 9 ልዩ ቦታው ቱሉ ሎላ በተካሄደው የከተማ ግብርና ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ላይ የአዲስ አበባ ብልፅግና ፅህፈት ቤት ሃላፊ አቶ ተስፋዬ በልጅጌ ተገኝተዋል።
 
አቶ ተስፋዬ በዚህ ወቅት የከተማ ግብርናን በማጠናከር በኮሮና ቫይረስ ሳቢያ ሊከሰት የሚችልን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ መቀነስ ይቻላል ብለዋል።
 
በከተማዋ የሚገኙ አርሶ አደሮችን የኑሮ ሁኔታ የተሻለ ለማድረግ ብሎም ለነዋሪዎቿ ምቹ እንድትሆን ለማድረግ ትኩረት መሰጡት ገልፀዋል።
 
ከዚህ በፊት በአርሶ አደሮች ላይ የተሰራው ስህተት አይደገምም ያሉት አቶ ተስፋዬ የብልጽግና ፓርቲ የአርሶ አደሩ የኑሮ ሁኔታ መሻሻል ላይ ይሰራል ብለዋል።
 
በአክሱማዊት ገ/ህይወት እና በሀይማኖት እያሱ
 
 
የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዘናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.