Fana: At a Speed of Life!

ባለስልጣኑ የነዳጅ ግብይት በሁሉም ባንኮች እንደሚጀመር አስታወቀ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 23፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በውስን የክፍያ አማራጮች ብቻ የነበረው የነዳጅ ግብይት በቀጣይ በሁሉም ባንኮች እንደሚጀመር የነዳጅና ኢነርጂ ባለስልጣን አስታውቋል።

የባለስልጣኑ የኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር በቀለች ኩማ እንዳሉት÷ ከነዳጅ ግብይትጋር በተያያዘ በተገልጋዮችና ሌሎች ባንኮች የሚነሱ ቅሬታዎችን ለመፍታት አገልግሎቱን ማስፋት አስፈልጓል፡፡

በዚህ መሰረትም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ በኦሮሚያ ኅብረት ሥራ ባንክ እና በቴሌ ብር ብቻ ሲደረግ የነበረው የነዳጅ ግብይት ዲጂታል የክፍያ አማራጮችን በማስፋት ሌሎች ተጨማሪ ባንኮች እንዲካተቱ ይደረጋል ብለዋል ።

ይህ አሰራር መተግበሩ ደንበኛው በተመቸው የክፍያ አማራጭ አገልግሎቱን እንዲያገኝ ያስችለዋል ነው ያሉት፡፡

አሰራሩን ለማስጀመር ረቂቅ እየተዘጋጀ መሆኑን ጠቁመው÷ ሥርዓቱ በቅርቡ ተጠናቅቆ ወደ ትግበራ እንደሚገባ አረጋግጠዋል፡፡

አሰራሩ ተግባራዊ ሲደረግም የነዳጅ ግብይቶችን ሪፖርት በአንድ ማዕከል ለመከታተል እንደሚያግዝ ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ተናግረዋል ።

በመሳፍንት እያዩ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.