Fana: At a Speed of Life!

በአዲስ አበባ ለሚካሄደው የድጋፍ ሰልፍ ለተሽከርካሪ ዝግ የሚሆኑ መንገዶች ይፋ ሆኑ

 

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 27፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ነገ በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በሚካሄደው የድጋፍ ሰልፍ ምክንያት ለተሽከርካሪ ዝግ የሚሆኑ መንገዶች ይፋ ተደርገዋል፡፡

በአዲስ አበባ የሚካሄደው የድጋፍ ሰልፍ በሰላም እንዲጠናቀቅ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት ማድረጉን የፀጥታና ደህንነት የጋራ ግብረ ሃይል አስታውቋል፡፡

የድጋፍ ሰልፉ ተሳታፊዎች ለጋራ ደህንነት ሲባል ፍተሻዎች እንደሚኖሩ ተገንዝበው ለፀጥታ አካላት የፍተሻ ሥራ ተባባሪ እንዲሆኑ ግብረ ሐይሉ አሳስቧል፡፡

በተመሳሳይ በሰልፉ ምክንያት የትራፊክ መጨናነቅ እንዳይፈጠር የተወሰኑ መንገዶች ለተሽከርካሪ ዝግ እንደሚሆኑም የአዲስ አበባ ፖሊስ ገልፆ አሽከርካሪዎች መረጃው ኖሯቸው ሌሎች አማራጭ መንገዶችን በመጠቀም ለትራፊክ ፖሊስ አባላት ትእዛዝ ተባባሪ እንዲሆኑ ተጠይቋል፡፡

በመሆኑም በዕለቱ ከንጋቱ 11፡00 ሰአት ጀምሮ የድጋፍ ሰልፉ እስኪጠናቀቅ ድረስ:-

– ከቴዎድሮስ አደባባይ በብሔራዊ ቴአትር ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ቴዎድሮስ አደባባይ፣
– ከኡራኤል አደባባይ ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ኡራኤል አደባባይ ላይ፣
– ከቦሌ አቅጣጫ ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው ኦሎምፒያ አደባባይ ላይና ታች እንዲሁም ግራና ቀኝ፣
– ከመስቀል ፍላወር ወደ ኦሎምፒያ የሚወስደው መንገድ ጋዜቦ አደባባይ ላይ፣
– ከጎተራ ማሳለጫ ወደ መስቀል አደባባይ አጎና ሲኒማ፣
– ከቅ/ቂርቆስ ቤ/ክርስቲያን በአዲሱ መንገድ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚሄዱ ለገሀር መብራት፣
– ከሜክሲኮ ወደ መስቀል አደባባይ ቴሌ ለሚጓዙ ለገሀር መብራት፣
– ከጌጃ ሰፈር አቅጣጫ ወደ መስቀል አደባባይ ለሚመጡ ተሽከርካሪዎች ሰንጋተራ ትራፊክ መብራት ላይ፣
– ከሃራምቤ መብራት ወይም ከአምባሳደር ሲኒማ ወደ መስቀል አደባባይ ሃራምቤ መብራት ላይ፣
– ከብሔራዊ ቤተ መንግስት ወደ መስቀል አደባባይ የሚወስደው መንገድ ብሔራዊ ቤተ መንግስት አጠገብ፣
– ከካዛንቺስ ሼል ወደ ባምቢስ የሚወስደው መንገድ ከዛንቺስ ሼል አጠገብ እንዲሁም
– ከጁፒተር ሆቴል ወደ ECA የሚወሰደው መንገድ ባምቢስ ሳልኮት ህንፃ አጠገብ ለተሽከርካሪ ዝግ ስለሚሆኑ አሽከርካሪዎች ይህንን ተገንዝበው አማራጭ መንገዶችን በመጠቀምና የትራፊክ ፖሊስ አባላት በሚጠቁሟቸው አቅጣጫ በመጓዝ አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ የአዲስ አበባ ፖሊስ ገልጿል፡፡

በተጨማሪም በተጠቀሱት መንገዶች ላይ ዋዜማው ምሽት 12 ሰዓት ጀምሮ እስከ ሰልፉ ፍፃሜ ድረስ ተሽከርካሪ አቁሞ መሄድ ወይም ማሳደር የተከለከለ ነው፡፡

ህብረተሰቡ ለፀጥታ ስጋት የሆኑ አጠራጣሪ ነገሮች ሲያጋጥሙት በ011-1-26-43-59፣ 011-5-52-63-02/03፣ 011-5-52-40-77፣ 011-5-54-36-78 እና 011-5-54-36-81 እንዲሁም በ987፣ 991 እና 816 ነፃ የስልክ ጥሪ ጥቆማ በመስጠትና አስፈላጊውን ትብብር በማድረግ የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ግብረ ኃይሉ ጥሪ አቅርቧል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.