Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያና ሞሮኮ ግንኙነታቸውን ለማጠናከር ተስማሙ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 12፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዴዔታ አምባሳደር ምስጋኑ አርጋ በሞሮኮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የሁለትዮሽ ጉዳዮች ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ፉዓድ ያዙሁር የተመራ ልዑክ ጋር ተወያይተዋል፡፡

በውይይታቸውም÷ ኢትዮጵያና ሞሮኮ ያላቸውን የሁለትዮሽ ግንኙነት ይበልጥ አጠናክሮ ማስቀጠል በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡

ሀገራቱ በተለይም ቀደም ሲል ስምምነት የደረሱባቸውን የንግድ፣ የኢንቨስትመንት፣ የፋይናንስ ፣ የአየር አገልግሎት እና የትምህርት ትብብር ስምምነቶች መልሶ በመቃኘት ለማጠናከር ተስማምተዋል።

ሀገራቱ ከሁለትዮሽ ግንኙነት ባለፈ በአህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ ሊተባበሩባቸው በሚችሉ መስኮችና ጉዳዮች ላይም ተወያይተዋል፡፡

በሁለቱ ሀገራት መካከል ቀደም ሲል የተደረጉ ከፍተኛ የእርስ በርስ ጉብኝቶች የሀገራት ጠንካራ ግንኙነት አንዱ መገለጫ መሆኑ በውይይቱ ተነስቷል፡፡

በጉብኝቶቹ ወቅት መግባባት ላይ የተደረሰባቸውን ስምምነቶች ወደ ተግባር ለመቀየር የሀገራቱ ባለድርሻ አካላት ትኩረት አድርገው በሚሰሩበት ሁኔታ ላይም የልምድ ልውውጥ ተደርጓል፡፡

ውይይቱን ተከትሎም በሞሮኮ እና ኢትዮጵያ መካከል የጋራ የሚኒስትሮች ኮሚሽን ስብሰባ በቅርቡ ለማካሄድ ስምምነት ላይ መደረሱን የሚኒስቴሩ መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.