Fana: At a Speed of Life!

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከጣልያን አቻቸው አድሚራል ጉሴፔ ካቮ ድራገን ጋር ተወያዩ

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከጣልያን አቻቸው አድሚራል ጁሴፔ ካቮ ድራገን ጋር ተወያዩ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 12፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከጣልያን ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም አድሚራል ጁሴፔ ካቮ ድራገን ጋር ተወያይተዋል፡፡

በፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ የተመራ የኢትዮጵያ የመከላከያ ልዑክ በጣልያን ወገን በተደረገለት ግብዣ በሀገሪቱ ይፋዊ የሥራ ጉብኝት እያደረገ ነው፡፡

የልዑካን ቡድኑ ጣልያን ሮም ሲደርስም በከፍተኛ ወታደራዊ ባለስልጣናት ደማቅ አቀባበል ተደርጎለታል።

በዛሬው ዕለትም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ከጣልያኑ አቻቸው አድሚራል ጁሴፔ ካቮ ድራገን ጋር በወታደራዊ ትብብሮች ዙሪያ ውጤታማ ውይይት አድርገዋል።

በውይይታቸውም÷ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ በሁለቱ ሀገራት መካከል እያደገ የመጣውን ግንኙነት አውስተዋል፡፡

ለዚህም ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በጣልያን ያደረጉት ጉብኝትና ጠ/ሚ ጆርጂያ ሜሎኒ በኢትዮጵያ ያደረጉት ይፋዊ የሥራ ጉብኝት ለሀገራቱ ግንኙነት መጠናከር አመላካች መሆኑን ጠቅሰዋል።

አድሚራል ጁሴፔ ካቮ ድራገን በቅርቡ በኢትዮጵያ ያደረጉት ጉብኝት በወታደራዊ ዘርፍ ያለውን ትብብር የበለጠ ለማጠናከር ጉልህ አስተዋጽኦ እንዳበረከተም ገልጸዋል።

አድሚራል ጁሴፔ ካቮ ድራገን በበኩላቸው÷በሁለቱ ሀገራት በተለያዩ ወታደራዊ ጉዳዮች ያለውን ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያላቸውን ፍላጎት ገልጸዋል።

በዘርፉ በተለያዩ ደረጃዎች ያለውን ግንኙነት ማስቀጠል እንደሚገባ አጽንኦት መስጠታቸውንም በጣልያን የኢትዮጵያ ኤምባሲ መረጃ ያመላክታል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.