Fana: At a Speed of Life!

ጠ/ሚ ዐቢይ ከመደመር መፅሃፍ ሽያጭ የተገኘውን 110 ሚሊየን ብር ለትምህርት ቤቶች ማሰሪያ አስረከቡ

አዲስ አበባ ፣ ነሐሴ 1 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ከመደመር መፅሃፍ ሽያጭ የተገኘውን 110 ሚሊየን ብር ለትምህርት ቤቶች ማሰሪያ አስረከቡ፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ገንዘቡን በቀዳማዊት እመቤት ፅህፈት ቤት ለሚገነቡ ትምህርት ቤቶች ማስገንቢያ ያስረከቡ ሲሆን ገንዘቡን ቀዳማዊት እመቤት ወይዘሮ ዝናሽ ታያቸው ተቀብለዋል፡፡

የመደመር መፅሃፍ የመጀመሪያ ገጽ ላይ ገቢው ሙሉ በሙሉ ለትምህርት ቤቶች ማሰሪያ እንደሚውል አስቀድሞ መገለጹ ይታወሳል፡፡

የቀዳማዊት እመቤት ፅህፈት ቤት በሃገር አቀፍ ደረጃ እስካሁን 20 ትምህርት ቤቶችን ያስገነባ ሲሆን ሰባቱ ሙሉ በሙሉ ተጠናቀዋል፤ 13ቱ ደግሞ ግንባታቸው ከ90 በመቶ በላይ የተጠናቀቀ ሲሆን በሚቀጥለው የትምህርት ዘመን ወደ ስራ ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ ገንዘቡን ባስረከቡበት ወቅት ከሽያጩ የተሰበሰበውን ገንዘብ መልሰን ለህዝብ ልማት ስናውል ከፍተኛ ኩራት ይሰማናል ብለዋል፡፡

መናገር ብቻ ሳይሆን የተናገርነውን ማድረግ እንደግለሰብም ሆነ እንደሃገር ልምድ እየሆነ ስለመምጣቱም አንስተዋል፡፡

በቀጣይም ከመደመር መፅሃፍ የሚገኝ አንድም ብር ቢሆን ለግለሰብ፣ ለፓርቲ አልያም ለመንግስት አይውልም ነው ያሉት፡፡

ገንዘቡ ሙሉ በሙሉ በትምህርት ዘርፍ ያለውን የማህበረሰብ ችግር ለመቅረፍ እንደሚውልም አረጋግጠዋል፡፡

የቀዳማዊት እመቤት ፅህፈት ቤት በበኩሉ የተገኘው ገንዘብ እስካሁን ከተገነቡት ትምህርት ቤቶች ውጭ ተጨማሪ ትምህርት ቤቶችን በሁሉም ክልሎች ለማስገንባት ይውላል ብሏል፡፡

በዓላዛር ታደለ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.