Fana: At a Speed of Life!

ፍርድ ቤቱ በአቶ እስክንድር ነጋ ላይ የዐቃቤ ህግ የቅድመ ምርመራ ምስክር እንዲሰማ በተከላካይ ጠበቃ ተወክለው እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ

አዲስ አበባ ፣ ነሃሴ 6 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ፍርድ ቤቱ በአቶ እስክንድር ነጋ፣ ስንታየሁ ቸኮል እና ቀለብ ስዩም ላይ የዐቃቤ ህግ የቅድመ ምርመራ ምስክር እንዲሰማ በተከላካይ ጠበቃ ተወክለው እንዲቀርቡ ለነሃሴ 8 ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጠ፡፡

ዛሬ ከሰአት በነበረው ችሎት በፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ የጊዜ ቀጠሮ ችሎት በልደታ አዳራሽ አቶ አስክንድር ነጋ፣ ስንታየሁ ቸኮል እና ቀለብ ስዩም ጉዳያቸው በችሎቱ ታይቷል።

ትናንት ዐቃቤ ህግ በችሎት ያቀረበውን የቀዳሚ ምርመራ መዝግብ ግልባጭ፣ የምስክሮቹን ዝርዝር እና የምስክሮችን ደህንነት ተጠብቆ ከአንደኛ እስከ 3ኛ ማንነታቸው ሳይታይ እንዲመሰክሩ እና ቀሪዎቹ ደግሞ በዝግ ችሎት ምስክርነታቸው እንዲሰማ አቤቱታ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡

በዚህም ተጠርጣሪዎቹ የቅድመ ምርመራ ምስክር ሊሰማ አይገባም ሲሉ ያቀረቡትን አቤቱታ ውድቅ ያደረገው ፍርድቤቱ ለዛሬ በዐቃቤ ህግ ከአንድ እስከ ሶሰት ያሉ ምስክሮች ሳይታዩ ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያሉ ምስክሮች ደግሞ በዝግ ችሎት ምስክርነታቸው ይሰማልኝ ባለው የምስክር አሰማም አቤቱታ ላይ ብቻ አስተያየታቸውን በፅሁፍ ይዘው ለዛሬ እንዲቀርቡ ፍርድ ቤቱ ትዛዝ መስጠቱ ማቅረባቸን የሚታወስ ነው።

በፅሁፍ የተቀበለው የተጠርጣሪዎችን አስተያየት ይዘትም በዋናነት ከ1 እስከ 3 ያሉ ምስክሮች ቁመናቸው ሳይታይ ስማቸው ሳይገለጽ ይመስክሩ መባሉ የመከላከል መብታችንን ይጎዳል እንዲሁም ቀሪ ምስክሮችም ቢሆኑ በዝግ ችሎት ሳይሆን በግልጽ ችሎት ምስክርነታቸውን ሊሰጡ ይገባል በምስክሮች ላይ ጉዳት አያስከትልም በማለት ዐቃቤ ህግ ማንነታቸው ሳይገለጽ እና በዝግ ምስክርነታቸውን ይስጥልኝ ብሎ ያቀረበው አቤቱታ ውድቅ ይደረግልን ሲሉ አስተያየቶቻውን በፅሁፍ አቅርበዋል።

በዚህ ላይ ምላሽ የሰጠው የፌደራል ጠቅላይ ዐቃቤ ህግም በምስክሮች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 699/2003 አንቀጽ 4 ላይ የተዘረዘሩ የተለያዩ የጥበቃ እርምጃዎች ውስጥ ለምስክሮች ደህንንት ማንነታቸው ሳይገለጽ ሳይታዩ እንዲሁም በዝግ ችሎት እንዲመሰከሩ መገለጹን አብራርቷል።

ምስክሮች ለደህንነታቸው ስጋት እንዳለባቸው መግለጻቸውን ተከትሎ በሰብአዊ መብት ጥሰት የተጠረጠሩት እነጌታቸው ሰአሰፋን ጨምሮ በሌላ በኩል ባለፉት 9 አመታት በአዋጁ መሰረት በቅድመ ምርመራ ምስክር በዝግ እና ማንነታቸው ሳይገለጽ ምስክርነት ሲሰጥ እንደነበር የሚታወስ ነው።

ዐቃቤ ህግም የቅድመ ምርመራ ማድረግ ማለት ምስክሮችን ማስረጃ ማቆየት ማለት መሆኑን ገልጾ ይህም የምስክሮችን ደህንነት ለማስጠበቅ በአዋጁ መሰረት የሚደረገው በዝግ ችሎት እና ማንነታቸው ሳይታይና ሳይገለጽ ምስክርነታቸውን እንዲሰጡ መደረጉ ተጠርጣሪዎች ላይ ጉዳት የሌለው መሆኑን አስረድቷል።

በዚህ መልኩ ባቀረበው አቤቱታ ፍርድ ቤቱ ተገንዝቦ ምስክርነት እንዲሰማ በመጠየቅ ተጠርጣሪዎቹ ያቀረቡት አቤቱታ ውድቅ እንዲደረግ ጠይቋል።

የህገ መንግስት ይጠየቅበት ተብሎ የተጣሰ ህገ መንግስት ጉዳይ እንደሌለም ተገልጻል።

ጉዳዩን የተከታተለው ፍርድ ቤቱ የዐቃቤ ህግ አቤቱታን በመቀበል ለምስክሮቹ ደህንነት ሲባል ማንነታቸው ሳይገለጽ እና በዝግ ችሎት ምስክርነታቸውን እንዲሰጡ ብይን ሰጥቷል፡፡

ይህን ተከትሎ አንደኛ ተጠርጣሪ አቶ እስክንድር ነጋ በዘር ማጥፋት ነው የተከሰስነው በማለት በዓለም አቀፍ ህግ መሰረት በዘር ማጥፋት የተከሰሰን በግልጽ ችሎት እንዲታይ ይደነግጋል ብለው ተከራክረዋል።

በግልጽ ችሎት ካልተመሰከረ ደግሞ ጠበቆቻችንን ይሰናበቱልን ሲሉ ፍርድ ቤቱ ጠይቀዋል።

እነ አቶ አስክንድር የተጠረጠሩት የእርስ በእርስ እና የሃይማኖት ግጭት በማስነሳት በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት ማድረስ ወንጀል መሆኑ ይታወሳል።

በተጠረጠሩበት በዚህ መዝገብ የምስክሮች ደህንነት ተጠብቆ የዐቃቤ ህግ ምስክርን እንዲሰማ ያዘዘው ፍርድቤቱ ምስክሮችን ለመስማት ለነሃሴ 8 ቀን 2012 ዓ.ም በተከላካይ ጠበቃ ተወክለው እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

በታሪክ አዱኛ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.