Fana: At a Speed of Life!

ደቡብ፣ ኦሮሚያና ጋምቤላን በአቋራጭ የሚያገናኘው የጎሬ – ማሻ- ቴፒ መንገድ ግንባታ ተጀመረ

አዲስ አበባ፣ ታህሳስ 11፣ 2012(ኤፍ.ቢ.ሲ) ሲጠናቀቅ ደቡብ፣ ኦሮሚያና ጋምቤላን በአቋራጭ የሚያገናኘው የጎሬ – ማሻ- ቴፒ የ140 ነጥብ 2 ኪሎ ሜትር የአስፋልት ኮንክሪት መንገድ ግንባታ ተጀመረ፡፡

ጅማ ፣ ቦንጋ ፣ ሚዛን ቴፒ ፣ ጋምቤላ ፣ ጎሬ ፣ መቱ እና አዲስ አበባን በአጭር ርቅት የሚያገናኘው የጎሬ – ማሻ- ቴፒ መንገድ ግንባታ የፌዴራልና የክልል ባለስልጣናት በተገኙበት በዛሬው ዕለት በይፋ ጀምሯል፡፡

ይህ የአስፋልት ኮንክሪት መንገድ ግንባታ በ4 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር እንደሚከናወን የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን የኮሙኒኬሽን ዳይሮክቶሬት አስታውቋል፡፡

ግንባታውን የደቡብ ኮሪያው ሃዮንዳይ ዴቨሎፕመንት ካምፓኒ የሚያከናውነው ሲሆን የመንገዱን ግንባታ የማማከር እና የቁጥጥር ስራውን ሱሶንግ ኢንጅነሪንግ ከሀገር በቀሉ ኔት ኮንሰልተንግ ኢጅነርስ በጋራ ያከናውኑታል ተብሏል፡፡

የመንገዱ ፕሮጀክት በገጠር 10 ሜትር ፣ በቀበሌ የእግረኛ መንገድ ጨምሮ 12 ሜትር ፣ በወረዳ የእግረኛ መንገድን ጨምሮ 19 ሜትር እና በዞን የእግረኛ መንገድን ጨምሮ  21 ነጥብ 5 ሜትር የጎን ስፋት እንደሚኖረው ተነግሯል፡፡

የስራ ተቋራጩ በአሁን ወቅት የቅድመ ዝግጅት ስራውን በማጠናቀቀ የግንባታ ስራውን መጀመሩ የተገለፀ ሲሆን  ግንባታው በ4 ዓመት ከስድስት ወር ውስጥ ይጠናቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ከዚህ ባለፈ ይህ የመንገድ ፕሮጀክት  ለአካባቢው ነዋሪዎች ማህበራዊ ፣ ፓለቲካዊ እና ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታዎች እንደሚኖሩት ተጠቁሟል፡፡

በይስማው አደራው

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.