Fana: At a Speed of Life!

መንግስት በትግራይ ክልል እያካሄደ ያለው ህግን የማስከበር ዘመቻ ነው- አቶ ዛዲግ አብረሃ

አዲስ አበባ፣ ሕዳር 10፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የፌደራል መንግስት በትግራይ ክልል እያካሄደ ያለው ህግን የማስከበር ዘመቻ መሆኑን በጠቅላይ ሚኒስትር ፅህፈት ቤት የዴሞክራሲ ማዕከል ግንባታ ሚኒስትር አቶ ዛዲግ አብርሃ ገለጹ።

አቶ ዛዲግ ከቢቢሲ ፎከስ ኦን አፍሪካ ሬዲዮ ጋር ባደረጉት ቆይታ፥ በትግራይ ክልል ውስጥ እየተካሄደ ያለው የህግ የበላይነትን የማስከበር እርምጃ ነው።

በኢትዮጵያ ውስጥ የእርስ በእርስ ግጭት የለም ያሉት አቶ ዛዲግ፥ የእርስ በእርስ ግጭት የሚባለው ቢያንስ በሰዎች መካከል ግጭት ሲኖር ነው ብለዋል፤ አሁን እየተወሰደ ያለው ህገ ወጡን የህሓት ጁንታ አባላትን ለህግ ለማቅረብ የሚደረግ ህግን የማስከበር እርምጃ መሆኑን በመጥቀስ፡፡

የትግራይ ህዝብ ከፌደራሉ መንግስት ጋር እየተጋጨ አይደለም ያሉት አቶ ዛዲግ፥ ይልቁንም የክልሉ ህዝብ በህገ ወጡ እና አምባገነኑ ቡድን አፈና ውስጥ ነው የሚገኘውም ብለዋል።

የክልሉ ነዋሪዎች ወደ ሱዳን እንዲሰደዱ እያደረገ ያለውም ይህ ህገ ወጥ ቡድን ነው ያሉት አቶ ዛዲግ፥ ይህን የሚያደርገውም ዓለም አቀፍ ትኩረትን ለመሳብ በማለም መሆኑንም ገልፀዋል።

“በስደት ወደ ሱዳን የሄዱት ዜጎቻችን ናቸው” ያሉት አቶ ዛዲግ፥ ስለዚህ የኢትዮጵያ መንግስት ዜጎቹን በሰላም ወደ ቤታቸው ለመመለስ ከሚመለከታቸው የሱዳን ባለስልጣናት ጋር በቅርበት እየሰራ መሆኑንም አረጋግጠዋል።

የኤርትራ ጦር ከኢትዮጵያ ሰራዊት ጋር ሆኖ ጥቃት እየሰነዘረብን ነው በሚል ለሚቀርበው ውንጀላም አቶ ዛዲግ በሰጡት ምላሽ፥ ይህ ከእውነት የራቀ ነው፤ የኢትዮጵያ መንግስት በአፍሪካ ጠንካራ ከሆኑ መንግስታት ወስጥ አንዱ ነው፤ የኢትዮጵያ ሰራዊት አቅምም ከኢትዮጵያ አልፎ ለሌሎች ሀገራትም የሚተርፍ ነው ብለዋል በምላሻቸው።

የኢትዮጵያ ሰራዊት በትግራይ ክልል ህግን ለማስከበር በቂ ነው ያሉት አቶ ዛዲግ፥ ስለዚህ የውጭ ሀገራት ድጋፍ አያስፈልግም ሲሉም ተናግረዋል።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.