Fana: At a Speed of Life!

በንጹሃን ዜጎች ላይ ጥቃት እያደረሱ የሚገኙ ታጣቂ ሀይሎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ ቀጥሏል – የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 9፣ 2013(ኤፍ ቢሲ) በተለያዩ አካባቢዎች በንጹሃን ዜጎች ላይ ጥቃት እያደረሱ የሚገኙ ታጣቂ ሀይሎች ላይ የሚወሰደው እርምጃ ተጠናክሮ መቀጠሉን የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አስታውቋል።
በተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በንፁን ዜጎች ላይ በሚደርሱ ጥቃቶች በርካቶች ህይወታቸውን አጥተዋል፣ ቤት ንብረታቸው ወድሟል አካባቢያቸውን ለቀው እንዲወጡ እና እንዲፈናቀሉ ሆኗል ተብሏል።
በተለይም በኦሮሚያ እና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ለፀጥታው ችግር መነሻ የሆኑት የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች ናቸው ብሏል የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ዛሬ በሰጠው መግለጫ ።
በኮሚሽኑ የወንጀል መከላከል ዘርፍ ሀላፊ ምክትል ኮሚሽነር ጀኔራል መላኩ ፈንታ በንፁሃን ዜጎች ላይ ፍፁም አረመኔያዊ የሆነ ድርጊት የሚፈፅሙት ታጣቂ ሀይሎች ተልዕኮ የተሰጣቸው እና ስምሪት ወስደው የሚንቀሳቀሱት ከህወሓት ቡድን እንደሆነ መታወቁን ተናግረዋል፡፡
ታጣቂ ሀይሎቹ የተደራጁ እና ከህብረተሰቡ ጋር ተቀላቅለው የፀጥታ ሀይል ባለበት ሁለት እና ሶስት በመሆን ትጥቃቸውን በመደበቅ በሽምቅ ጉዳት የማድረስ ስራ እየሰሩ በመሆኑ የሚከተሉት ስልትም አስቸጋሪ መሆኑን ነው ምክትል ኮሚሽነሩ የተናገሩት።
ፌዴራል ፖሊስ ከክልል የፖሊስ እና ከመከላከለያ ጋር በጋራ እየሰራ እንደሆነ በኮሚሽኑ የወንጀል ምርመራ ዘርፍ ሀላፊ ምከትል ኮሚሽነት ጀኔራል ዘላለም መንግስቴ ገልጸዋል።
በወለጋም ሆነ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በታጣቂ ሀይሎቹ ላይ እርምጃ እየተወሰደባቸውሲሆን፥ በመተከል 3 ሺህ ታጣቂዎች፣ ከ 900 በላይ ዘመናዊ የጦር መሳሪያዎች እና ከ1 ሺህ በላይ ቀስት እና የመሳሰሉ ባህላዊ የጦር መሳሪያዎች ተይዘዋል።
ከህግ ማስከበሩ ጋር ተያይዞም በትግራይ ክልል የፀጥታ ሀይሉ በሰራው ስራ ከ270 በላይ ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር የዋሉ ሲሆን 72 ያህሉ የክልሉ አመራሮች የነበሩ ወደ ማረሚያ ቤት እንዲወርዱ ተደርገዋልም ነው ያሉት ምክትል ኮሚሽነሩ።
በማይካድራ ንፁሃንን በመጨፍጨፍ ከሚፈለጉ 260 ግለሰቦች ውስጥ 137ቱ በቁጥጥር ስር መዋላቸው የተገለፀ ሲሆን፥ ቀሪዎቹ ከሀገር በመሸሽ በስደተኛ መጠለያ ውስጥ የሚገኙ በመሆናቸው በተለይም በሱዳን የስደተኛ መጠለያ የሚገኙትን ለመያዝ እና ወደ ህግ ለማቅረብ የሚያስችል ሰነድ ተዘጋጅቷል ብለዋል።
የፀጥታ ችግሩን ሙሉ በሙሉ ለመፍታት እና በተለይም በታጣቂ ሀይሎች እየደረሰ ያለውን ጥቃት ለመከላከልም ህብረተሰቡ አብሮ እንዲሰራ እና ተቀላቅለው የሚንቀሳቀሱትን በማጋለጥም የበኩሉን እንዲወጣም ጥሪ ቀርቧል፡፡
በሌላ በኩል ኮሚሽኑ የፀጥታ ስጋት ያለባቸው ቦታዎችን ጨምሮ ስድስተኛው ሀገራዊ ምርጫን በተሳካ ሁኔታ እንዲፈፀም ለማድረግ የሚያስችል ዝግጅት ማድረጉን ገልጿል፡፡
ህገ ወጥ የሰዎች፣ የገንዘብ እና የኮንትሮባንድ ዝውውርን በሚመለከትም ከጉምሩክ እና ግብር ስወራ ጋር ተያይዞ በመንግስት ላይ ሊደርስ የነበረን 24 ቢሊየን ብር ኪሳራ ማዳን ተችሏል።
እንዲሁም 1 ነጥብ 7 ቢሊየን ብር የሚያወጡ ገቢ እና ወጪ ኮንትሮባንድ እቃዎች ሲያዙ፥ የድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎችን ለመከላከልም በተለይ ከጅቡቲ፣ ደቡብ ሱዳን እና ሶማሊያ ጋር የጋራ መግባባት ላይ ተደርሶ በቅርቡ ወደ ስምሪት ይገባል ብለዋል፡፡
በዙፋን ካሳሁን
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡-https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.