Fana: At a Speed of Life!

የዐቃቤ ህግ በእነ ጃዋር መሀመድ ላይ በዝግ ችሎት ምስክር ላሰማ ጥያቄ ውድቅ ሆነ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 28፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የዐቃቤ ህግ በእነ ጃዋር መሀመድ ላይ በዝግ ችሎት ላሰማ ያለው የምስክር የአሰማም ሂደት ጥያቄ ውድቅ ሆነ፡፡

ዐቃቤ ህግ ባለፈው ቀጠሮው በምስክር ጥበቃ አዋጅ መሰረት ለምስክሮቼ ደህንነት ሲባል ከመጋረጃ በስተጀርባ እና በዝግ ችሎት ምስክሮቼን ላሰማ ሲል አቤቱታ አቅርቦ ነበር፡፡

ተከሳሾቹም የመከላከል መብታችንን የሚገድብ እና የዐቃቤ ህግ አቤቱታ ታማኝነት የለውም በማለት የዐቃቤ ህግ አቤቱታ ውድቅ እንዲደረግ ማመልከታቸው ይታወሳል።

በዚህ መሰረት የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አንደኛ የጸረ ሽብርና የህገ መንግስት ጉዳዮች ወንጀል ችሎት ጥያቄውን መርምሮ ውድቅ አድርጎታል፡፡

ችሎቱ በዛሬው እለት ተሰይሞ አቶ ጃዋር መሀመድን ጨምሮ ሁሉም ተጠርጣሪዎች በተገኙበት ጉዳያቸውን ተመልክቷል፡፡

በዚህም ዐቃቤ ሕግ ባለፈው ቀጠሮ በምስክር ጥበቃ አዋጅ 699/2003 አንቀጽ 4 /1 ሸ እና ቀ መሰረት  ለ146 ምስክሮች ጥበቃ ተደርጓል ብሎ ከመጥቀስ በዘለለ ምስክሮች ላይ የሚደርሰውን ጉዳት በማስረጃ ያላስደገፈ በመሆኑ በቂ ምክንያት ሆኖ አላገኘሁትም ሲል ፍርድ ቤቱ ምስክሮቹ በግልጽ ችሎት ምስክርነታቸውን እንዲሰጡ ብይን ሰጥቷል።

ይሁን እንጂ ተከሳሾቹ የምስክር ዝርዝር ይገለጽልን ብለው ያቀረቡት አቤቱታን በተመለከተ ግን ፍርድ ቤቱ የምስክር ዝርዝር ለምስክሮች ደህንነትና መብት ጥበቃ ሲባል የምስክሮች ማንነት እንዳይገለጽ ሲል ጥያቄውን ውድቅ አድርጎታል።

በዚህም መሰረት የምስክሮች ዝርዝር ሳይገለጽ ምስክርነታቸው በግልጽ ችሎት እንዲሰማ ሲል ፍርድ ቤቱ  ብይን ሰጥቷል።

በተጨማሪም ሁሉም ተከሳሾች የጠየቁት የዋስትና ጥያቄ ውድቅ ተደርጎ የአቃቤ ህግ ምስክርን ለመስማት ለሚያዝያ 5 ቀን 2013 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል።

በታሪክ አዱኛ

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.