Fana: At a Speed of Life!

ከግድቡ ግንባታ ጋር ተያይዞ ግብጽና ሱዳን ባለሙያ እንዲሰይሙ መጋበዛቸው የዲፕሎማሲውን ጥረት ጫፍ ያደረሰ ነው -ፕሮፌሰር ያዕቆብ አርሳኖ

አዲስ አበባ ፣ ሚያዝያ 5 ፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) የሁለተኛው ዙር የውሃ ሙሌት ከመጀመሩ በፊት መረጃ ለመለዋወጥ የግድብ ተወካዮቻቸውን እንዲሰይሙ ኢትዮጵያ ለግብጽና ሱዳን ያቀረበችው ጥያቄ የዲፕሎማሲውን ጥረት ጫፍ ያደረሰ እና ኢላማውን በአግባቡ የመታ መሆኑን ፕሮፌሰር ያዕቆብ አርሳኖ ገለጹ።

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካ ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህርና የዓባይ ውሃ ጉዳይ ተመራማሪ ፕሮፌሰር ያዕቆብ አርሳኖ ÷ለሃገራቱ የቀረበው ጥያቄ በዲፕሎማሲው መስከ የተደረገውን ጥረት የመጨረሻው ነጥብ ያስቆጠረ ነው ብለዋል።

ከአሁን በፊት በተደጋጋሚ የግብጽና የሱዳን ባለሙያዎች እንዲሁም የሱዳን መሪም ጭምር የህዳሴ ግድቡ ያለበት ቦታ ድረስ ሄደው ሲያዩና ሲከታተሉ እንደነበር አስታወሰዋል።

አሁንም ሁለቱ ሃገራት ባለሙያዎቻቸውን እንዲሰይሙ ሲጋበዙ የመጀመሪያ እንዳልሆነ አመልክተዋል፡፡

አሁንም ሁለተኛው ዙር የውሃ ሙሌት ከመጀመሩ በፊት ሁለቱ ሃገራት ባለሙያዎቻቸውን እንዲሰይሙ ኢትዮጵያ ጥሪ አቅርባለች ብለዋል።

ይህ ደግሞ ከዚህ ቀደምም ሲያዩ እንደቆዩ ሁሉ አሁንም ቢሆን በኢትዮጵያ በኩል በድብቅ የሚሰራ ሥራ አለመኖርን የሚያሳይ መሆኑን አመላክተዋል።

ግድቡ እየተገነባ ከቆየ በኋላ ደግሞ ግንባታው እንዲስተጓጎል ጥረዋል፣ቀጥሎም የግድቡ ስራ እየተጠናቀቀ መሄዱን ሲረዱ  በአግራሞት ሲመለከቱ ከርመዋል ነው ያሉት፡፡

በአሁን ደረጃ የኢትዮጵያ መንግስት ግብጽና ሱዳን የግድብ ባለሙያዎችን  እንዲሰይሙ መፍቀዱ ከዲፕሎማሲው ሙያ አንጻር ሲስተዋል ኢትዮጵያ ዲፕሎማሲውን ከፍተኛ ደረጃ ላይ ማድረስ መቻሏ አመላካች ሆኗልም ብለዋል፡፡

“የህዳሴ ግድቡ ለኢትዮጵያ የሚጠቅም መሆኑን ስንነግራቸው እንደቆየንና ለሁለቱም ሃገራት ከዚህ ቀደም ሲነገራቸው እንደቆየው ሁሉ አሁንም ባለሙያዎችን እንዲመድቡ መጋበዛቸው እነሱንም በከፋ መንገድ የማይጎዳ መሆኑ ግልጽ እንዲሆንላቸው ከሚል ሐሳብ የመጣ” መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

ፕሮፌሰር ያዕቆብ አሁን በህዳሴ ግድቡ ዙሪያ ብዙ ጫጫታ ባለበት በዚህ ሁኔታ እንኳ ውሃው ከመሞላቱ በፊት ባለሙያ ሰይሙ ብሎ ማለት በኢትዮጵያ በኩል የታየ ልበ ሙሉነትና ሆደ ሰፊነት መሆኑን አመላካች ነው ማለታቸውን ኢፕድ ዘግቧል።

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/

ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting

ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/

ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision

ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡

ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.