Fana: At a Speed of Life!

የአሸባሪው ቡድን ቤቶች ላይ ከባድ መሳሪያ ጭምር በመተኮስ ነዋሪው እንዲሸሽ አድርጓል

አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 3፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ)የአሸባሪው ሀወሓት ቡድን ደብረ ዘቢጥ ከተማን ሙሉ ለሙሉ በያዘበት ወቅት ቤቶች ላይ ከባድ መሳሪያ ጭምር በመተኮስ ነዋሪው እንዲሸሽ ማድረጉ ተገለጸ::

ወይዘሮ ዘውዲቱ ጎበና በሰሜን ወሎ ዞን የመቄት ወረዳ ደብረ ዘቢጥ ከተማ ነዋሪ ናቸው::

አሸባሪው ቡድን ከተማዋን በመውረሩ ሀብት ንብረታቸውን ጥለው ወደ ቆላማ አካባቢ ባሉ ዘመዶቻቸው ተጠግተው እንደነበር ይናገራሉ::

የእርሳቸው ባለቤት ከቀናት በኋላ ወደ ቀዬው ተመልሰው ስንቅ ሊያመጡ ሲሉ በአሸባሪዎች እንደተገደሉባቸውም ይገልጻሉ::

ለስንቅ ብለው የወጡትን ባለቤታቸውን በጥይት በማጣታቸው ወደ መኖሪያቸው ተመልሰው ኀዘን ተቀምጠዋል::

ለወትሮ ቢሆን በሃዘንም በደስታም በሰዎች የሚሞላው ቤታቸው ወና ሆኗል::

ብዙዎች ከከተማዋ ለቀው ስለወጡና ስላልተመለሱ የኀዘን ተካፋይ ማግኘት አለመቻላቸውን ኢፕድ ዘግቧል::

ከውስን ቤተሰቦቻቸው ጋር በባዶ ቤት ሆነው የአሸባሪውን በደል በማስታወስ ሃዘናቸውን ይገልጻሉ::

ይህ ክፉ ጠላት ሀብትና ንብረት መዝረፉና ማውደሙ ሳያንስ የንጹሀንን ነፍስ እንዳሻው ሲያጠፋ እንደነበር ወይዘሮ ዘውዲቱ ይናገራሉ::

ዛሬ ላይ ቤተሰቦቻቸው ዘመድ ቤት ቢሆኑም ወቅቱ እንኳንስ ዘመድ አስጠግቶ ማኖር ይቅርና የራስን ቤተሰብም ለመምራት አስቸጋሪ ነው በማለት፤ አሸባሪ ቡድን ያደረሰውን በደል መቼውንም አንረሳውም ብለዋል::

በደብረ ዘቢጥ ከተማ ወይን ሰፈር ነዋሪ የሆኑት ቄስ መርሻ ብርሃኔ እንደሚሉት፤ የአሸባሪው ሀወሓት ቡድን ከተማዋን ሙሉ ለሙሉ በያዘበት ወቅት ቤቶች ላይ ከባድ መሳሪያ ጭምር በመተኮስ ነዋሪው እንዲሸሽ አድርጓል::

እያንዳንዱ ነዋሪ ሸሽቶ በመውጣቱ የግለሰቦችን ቤት እንደ መኖሪያ ሲጠቀሙበት ነበር::

ቤት ውስጥ ያለውን ከዱቄት እስከ ቁም ከብት ያገኙትን ዘርፈው በልተዋል::

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.