Fana: At a Speed of Life!

በድሬዳዋ አስተዳደር ለ63 ሺህ ሰዎች የኮሮና ቫይረስ መከላከያ ክትባት መስጠት ተጀመረ

 

አዲስ አበባ፣ ህዳር 7፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ለ63 ሺህ ሰዎች የኮሮናቫይረስ መከላከያ ክትባት በየቀበሌው የመስጠት ዘመቻ መጀመሩን የአስተዳደሩ ጤና ቢሮ አስታወቀ።

የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር ከንቲባና የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች ዛሬ በተጀመረው የክትባት ዘመቻ ኅብረተሰቡ ተጠቃሚ እንዲሆን ጥሪ አቅርበዋል፡፡

ከዛሬ ጀምሮ ለሚቀጥሉት 10 ቀናት በአስተዳደሩ ገጠርና ከተማ በሚገኙ ቀበሌዎች መሰጠት በተጀመረው የክትባት ዘመቻ የጤና ባለሙያ ቡድኖች በጤና ተቋማትና በየሰፈሩ በመዘዋወር ክትባቱን እየሰጡ ነው፡፡

የድሬዳዋ ጤና ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ዩሱፍ ሰኢድ ለኢዜአ እንደገለጹት፥ የኮሮናቫይረስ ወረርሽኝ የሚያደርሰውን ሁለንተናዊ ቀውስ ለመከላከል በነፃ እየተሰጠ ያለውን ክትባት መጠቀም ተገቢ ነው፡፡

ከዛሬ ጀምሮ ለ10 ቀናት በዘመቻ የሚሰጠው ክትባት በውጤት እንዲጠናቀቅ አስፈላጊው ግብዓትና የሰው ኃይል ከማሟላት ባለፈ አሠራር ተዘርግቶ ወደ ሥራ መገባቱን ኢዜአ ዘግቧል።

ክትባቱን መውሰድ በሽታውን የመከላከል አቅም በከፍተኛ ደረጃ ስለሚጨምር ህብረተሰቡ ሳይዘናጋ ተጠቃሚ እንዲሆን አሳስበዋል።

የክትባቱን ዘመቻ ያስጀመሩት የድሬዳዋ አስተዳደር ከንቲባ ከድር ጁሃር በበኩላቸው እንዳሉት፥ “የኮሮና ቫይረስ ከፍተኛ ሰብዓዊ ጉዳት አስከትሏል፤ የሀገርን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴንም ክፉኛ ጎድቷል” ፡፡

ክትባቱ እነዚህን ችግሮች በማስቀረት አምራችና ጤናማ ኅብረተሰብ ለመፍጠር የሚደረገውን ጥረት ስለሚያግዝ ህብረተሰቡ በነቂስ ወጥቶ እንዲከተብ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

አካባቢዎን ይጠብቁ!
ወደ ግንባር ይዝመቱ!
መከላከያን ይደግፉ!

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.