Fana: At a Speed of Life!

የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ብሔር ብሄረሰቦች ጋር በመሆን ጸረ ኢትዮጵያ ኃይሉን መቅጣቱን ይቀጥላል – የአማራ ብልጽግና ፓርቲ

አዲስ አበባ፣ ሃምሌ 27፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ)የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ብሔር ብሄረሰቦች ጋር በጋራ ቁሞ ጸረ ኢትዮጵያ ኃይሉን ያለምህረት መቅጣቱን እንደሚቀጥል የአማራ ብልጽግና ፓርቲ አስታወቀ፡፡

የክልሉ ብልጽግና ፓርቲ መግለጫ እንደሚከተለው ይቀርባል፡፡

ትውልዱ የአባቶቹን አደራ ይወጣል!

ይህ ጦርነት የኢትዮጵያን ህልውና የማረጋገጥና ሀገራዊ ክብሯን ከፍ የማድረግ ጉዳይ ነው! ይህ ጦርነት የትውልድ አደራን የመወጣት ብሔራዊ ተልዕኮ ነው። እኩልነትን የመቀበልም ሆነ የመለማመድ አንዳች ፍላጎት የሌለውን እቡይ ቡድን፣ ከእነ ትዕቢቱ ወደመቃብር የማውረድ ጉዳይም ነው። ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነት ከተጋረጠባቸው የህልውና አደጋ የማሻገር ብሎም ከፍ የማድረግ ተልዕኮ አለው። ጦርነቱ ኢትዮጵያና ልጆቿን ከቀጥተኛ የህልውና አደጋ ነጻ የማድረግ ጉዳይ ነው። ከመዳከም ወደ ብርታት፣ ከመከፋፈል ወደ አንድነት፣ ከጠባቂነት ወደ ራስ-በቅነት፣…የምንሻገረው የኢትዮጵያ ካንሰር የሆነውን አሸባሪውን ትህነግ ቆርጠን መጣል ስንችል ነው።

ትህነግ ከአገዛዝ መነሻው በተዳከመች ኢትዮጵያ አማራ ጠል የአናሳ አገዛዝ ሥርዓት ለማጽናት ኢትዮጵያዊነትን ማራከስ የትግሉ አካል አድርጎት ኑሯል። ስለኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነት ክብር ብዙዎቹ የኢትዮጵያ ልጆች መዋደቃቸው የታሪክ እውነታ ቢሆንም፣ ኢትዮጵያዊነትን የአንድ ወገን ጉዳይ አስመስሎ መርዙን ሲረጭ ኑሯል። የምኞቱን ያህል ባይሳካለትም ኢትዮጵያዊነትን አደብዝዞት ቆይቷል።

ኢትዮጵያ በብዝሃ ባህል፣ ቋንቋና ትውፊት የደመቀች መሆኗ እንደበጠበቀ ሁኖ ከቋንቋ ማንነት ከፍ ብላ ለሁሉም ልጆቿ የጋራ ጥላና ከለላ እንዳትሆን በሴራና በመርዛማ ትርክቶቹ ታትሯል። ቅራኔ ሲፈለፍል ውሎ ያድር የነበረው አሸባሪው ትህነግ፣ የሌሎች የእርስ በርስ ግጭት የእርሱ ሥልጣን ማስቀጠያ ገመድ ነበር።

ይህ ለባዕድ ሥርዓት የመታመን ታሪክ ከነበራቸው አያት ቅድመ-አያቶቹ የወረሰው ፕሮችስካዊ መስመር የማታ ማታ ዋጋ አስከፍሎታል። ዛሬ የኢትዮጵያን ማደግና መቀየር ከማይመኙ ጥቂት የውጭ ኃይሎች በስተቀር በሀገር ውስጥ አንድም አጋር ማግኘት ያልቻለው የቀደመ ክፋቱ ብድራት ሁኖበት ነው። ሁሉም የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች ሊወጉት በጋራና በአንድነት የቆሙት የህልውናቸው አደጋ መሆኑ ስለገባቸው ነው።

ትላንት በሞግዚት አስተዳደሩ የጌታና ሎሌ ግንኙነት (patron-client relations) ዘላቂ የአመራር ዘይቤ እንዲሆን እንጅ የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች የጋራ አመራር ፈጥረው በጋራ እንዲቆሙ ፍላጎት አልነበረውም። ይልቁንስ አንዱ በሌላው ወንድሙ እንዲነሳ በማድረግ ራሱን የመሀል ዳኛ አድርጎ በቅራኔ የበላይነት ፖለቲካውን ሲሰራ ኑሯል። ደም በማፍሰስ ግብሩ ኢትዮጵያ ላይ የሰብዓዊ ልማት ድቀት ፈጥሯል። ‘በመንገዴ ላይ ቁመዋል’ ያላቸውን የነጻነት ታጋዮች፣ ፍትሕ ጠያቂዎችን ከየብሄረሰቡ ፈጅቷል። በደመቀዝቃዛ ግብሩ ደም ያላፈሰሰበት የኢትዮጵያ ግዛት፣ በደል ያልፈጸመበት ብሄረሰብ የለም። አሁንም የጥፋት ታሪኩን በሌላ መንገድ እየተገበረው ነው።

አሸባሪው ትህነግ፣ “ኢትዮጵያ ትውደም እኛ እንቅደም” በሚል አስተምህሮ ያጠመቃቸው የጥፋት ደቀ-መዝሙሮቹ በርግጥም የኢትዮጵያና ልጆቿ ጠላቶች መሆናቸውን በተግባር እያስመሰከሩ ነው። የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች ውህድ ማንነት አካል የሆነው መከላከያ ሠራዊታችን፣ አልፎም የአማራና የአፋር ሕዝብን እየወጉ ያሉት እንደሬሽን በታደሉት የጸረ-ኢትዮጵያ አስተምህሮታቸው መሠረት ነው። ጸረ-ኢትዮጵያ አቋም የትግራይ ጥቅም ማስጠበቂያ የፖለቲካ መርህ ተደርጎ የተወሰደው በዚህ ባህሪው ነው። ከዲያስፖራ እስከ ሀገር ቤት፣ ከእረኛ እስከ ምሁር በደጋፊዎቹ ተይዞ ያለው የፖለቲካ ፍላጎት “ኢትዮጵያ ትድማ እኛ እንልማ” ነበር። ነገር ግን በነጻነት፣ እኩልነትና ፍትሐዊ ተጠቃሚነት በሚያምኑ የኢትዮጵያ ልጆች የጋራ ትግል ይህ የፖለቲካ ፍላጎቱ ተቀልብሷል። በመሆኑም “ኢትዮጵያን አፍርሰን ታላቋ ትግራይ እንመሰርታለን” ወደሚል የቀደመ ስውር ፍላጎት መገለጥ ስለመጀመሩ በአደባባይ ጩኸታቸው ብቻ ሳይሆን መሬት ወርደው በሚሰሯቸው ተግባራት በግልጽ የሚታዩ ናቸው።
ይህ እኩልነትን ሳይሆን የበላይነት፣ በፍትሐዊ ተጠቃሚነት ሳይሆን በሁለት እጅ ብልጫ፣… የሚያምን፣ በኢትዮጵያ ደምና ሀብት ታላቋን ትግራይ የመመስረት እቅዱን የማያፍርበት፣ ካለፈው ስህተቱ የመማር አንዳች ፍላጎት የሌለው የጥፋት ቡድን ጨርሶ ሊደመሰስ ይገባል። እንኳንስ ድርጅቱ አስተሳሰቡ በራሱ ነፍስ ሊዘራ አይገባም።

ይህ ወቅት ከአድዋ ድል በፊት፣ እንዲሁም በዳግማው የጣሊያን ወረራ ጊዜ እንደነበረው የጭንቅ ዘመን የሚመሰል ነው፡፡ በሁለቱም ወቅቶች የቅኝ ገዥ ተስፋፊ ኃይሎች ኢትዮጵያ እንድትጠቃ ሰበብ የፈለጉበት፣ ጠላትን ያገዙበት፣ የኢትዮጵያንና የአማራን ስም በክፉ ያነሱበት ብሔራዊ አደጋ የደቀኑበት ወቅት ነበር፡፡ ዛሬም ያለንበት ሁኔታ ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ በአድዋ የተሸነፈው ጣሊያን ከአርባ አመት በኋላ ሲመጣ አማራን ስሙን እያጠፋ፣ ሌሎችን የጨቆነ አስመስሎ በዓለም መድረክም ለኢትዮጵያውያንም የተሳሳተ ትርክትና መረጃ በማቀበል ነው። ትህነግም ሥልጣኑን ካጣ በኋላ ልክ እንደ ጣሊያን አማራን በዓለም አቀፍ ደረጃም ለኢትዮጵያውያንም እየረገመ፣ ከፋፍሎ ለማጥቃት ቢሞክርም የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች እውነታው ገብቷቸው ከእርሱ በተቃራኒ በጋራ ቁመዋል። በሀገር ውስጥ አንዳች አጋር ያጣው አሸበሪው ትህነግ በኢትዮጵያ ታሪካዊ ጠላቶች ትክሻ ላይ መንጠልጠል ቢመርጥም ትውልዱ የአባቶቹን አደራ መወጣቱ ጥርጥር የለውም!

አማራና ኢትዮጵያ ላይ ጥላቻ ቋጥሮ፣ በአዲስ ጉልበት ለወረራ የመጣው አሸባሪው ትህነግ ዕድሉን ቢያገኝ በጣሊያን ወረራ ዘመን ከደረሰው ውድመት በላይ እልቂት ከመፈጸም ወደ ኋላ አይልም። የዘመናችን “የካቲት 12” ማይካድራ ላይ ተፈጽሞ አይተናል። ይህን የጥፋት ኃይል በጽናት ካልተዋጋነው ከተሞቻችን በሙሉ የማይካድራን ዕጣ ከማስተናገድ አይተርፉም።

ይህ የታሪክ አዙሪት ሊሰበር ይገባል፡፡ አዙሪቱን ለመስበር ደግሞ ኃላፊነቱ በእኛ ትውልድ ትክሻ ላይ ወድቋል፡፡ አሁን ዋናው ጥያቄ በዳግማዊ የጣሊያን ወረራ ወቅት፣ እንዲሁም ከ1983 ጀምሮ በአማራም በኢትየጵያም ላይ ከተፈፀመው የባሰ በደል እንዲፈፀም ቆመን እናያለን? ወይንስ አዙሪቱን ለመስበር በቁርጠኝነት እንፋለማለን? የሚለው ነው፡፡

ትህነግ ዳግም ዕድል ካገኘ በእያንዳንዳችን ላይ የጥላቻው በትር እንዲያርፍ ፈቅደናል ማለት ነው። ወንድ ልጆቻችን እንዲኮላሹ፣ ሴቶቻችን እንዲደፈሩ፣ በየከተማው ከማይካድራ የባሰ የዘር ጭፍጨፋ እንዲፈፀም ካልፈለግን ትህነግን በቁርጠኝነት መታገል አለብን፡፡ ይህ ነው የትውልዱ አደራ።

በአድዋ ድል የምንኮራው አባቶቻችን ለመወረር፣ ለመዋረድ ፍቃደኛ ባለመሆናቸውና በጽኑ ቁርጠኝነት ታግለው በማሸነፋቸው ነው። በሚያዚያ 27 የአርበኞች ድል የምንኮራው፤ በአንጻሩ ባንዳና የባንዳ ቤተሰቦች ሲያፍሩ የሚኖሩት አርበኞቻችን ለአምስት አመት በዱር ገደል ታገለው ትርጉም ያለው መስዋዕትነት በመክፈላቸው ነው። በአስር ሺህዎች ተሰውተው ኢትዮጵያ በአፍሪካም ሆነ በዓለም መድረክ የነጻነት ተምሳሌታዊ ታሪኳን አስጠብቀዋል። አባት አርበኞቻችን ወራሪው ፋሽስት ጣሊያን በኢትዮጵያ ዕጣ ፈንታ ላይ እንዲወስን ዕድል አልሰጡትም። እናም ዛሬም ሆነ ነገ ጥንተ-ጠላት የሆነው ትህነግ በእኛ ላይ እንዲወስን መፍቀድ የለብንም። በአስተሳሰብም ሆነ በገቢር ጸረ-አማራ እና ጸረ-ኢትዮጵያ ስለመሆኑ በተግባር የተፈተሸ መራር እውነታ በመሆኑ ከባዕድ ወራሪ ተለይቶ ሊታይ አይችልም።

ስለሆነም የአማራ ሕዝብ ከሌሎች ወንድም የኢትዮጵያ ብሔር ብሄረሰቦች ጋር በጋራ ቁሞ ጸረ ኢትዮጵያ ኃይሉን ያለምህረት መቅጣቱን ይቀጥላል። ለኢትዮጵያ ህልውና እና ክብሯን ለማስጠበቅ በትግል ዓላማው ጸንቶ ይታገላል።

በርግጠኝነት ትውልዱ የአባቶቹን አደራ ይወጣል።

ኢትዮጵያዊነት ያስተማረን እውነታ በጊዜያዊ ችግር ተሸንፎ መውደቅ ሳይሆን ፈተናዎችን ወደ እድል እና መልካም አጋጣሚ ቀይሮ ለታሪክ የሚበቃ ድል መቀዳጀት ነው። የአማራ ሕዝብም ከወንድሞቹ ጋር በፈጠረው የተባበረ ክንድ የኢትዮጵያን ካንሰር ቆርጦ ይጥላል። በአሸባሪው ትህነግ መቃብር ላይም በጠንካራ ወንድማማችነት ዴሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን በጋራ ይገነባል!!

ትውልዱ የአባቶቹን አደራ ይወጣል!

የአማራ ብልጽግና ጽ/ቤት

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.