Fana: At a Speed of Life!

በኢትዮጵያ ባለፉት 15 ቀናት የኮሮና ቫይረስ ስርጭት በ310 በመቶ ጨምሯል

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 24 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) በኢትዮጵያ ባለፉት 15 ቀናት የኮሮና ቫይረስ ስርጭት በ310 በመቶ መጨመሩን የኮቪድ19 ወረርሽኝ መከላከልና መቆጣጠር የሚኒስትሮች ኮሚቴ አስታወቀ።

የኮቪድ19 ወረርሽኝ መከላከልና መቆጣጠር የሚኒስትሮች ኮሚቴ አስተባባሪ ሴክሬታሪያት እና የሰላም ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪሃት ካሚል የኮሚቴውን መደበኛ ውይይት በማስመልከት መግለጫ ሰጥተዋል።

በመግለጫቸውም ባለፉት 2 ወር ከ4 ቀናት ውስጥ 53 ሺህ 600 ሰዎች ተመርምረው 286 ሰዎች እንዲሁም ባለፉት 15 ቀናት 55 ሺህ 845 ሰዎች ተመርምረው 886 ሰዎች ቫይረሱ እንደተገኘባቸው አንስተዋል።

ይህም በተጠቀሱት ቀናቶች የቫይረሱ ስርጭት በ310 በመቶ ማደጉን እንደሚያሳይ ገልጸዋል።

አሁን ላይ የህብረተሰቡ የመረዳዳት ባህል እያደገ መምጣቱን ያነሱት ወይዘሮ ሙፈሪሃት፥ ህብረተሰቡ አሁን ያለው የወረርሽኙ ስርጭት አሳሳቢ መሆኑን በመረዳት የፀጥታ አካላትን በራሱ ተነሳሽነት ማገዝ ይኖርበታል ብለዋል።

ከአዲስ አበባ ጋር ተያይዞ ከተማዋ ከአራቱም አቅጣጫ ሰዎች የሚገቡባትና የሚወጡባት በመሆኑ የቫይረሱ ስርጭት እንዳይስፋፋ ህብረተሰቡ ተገቢውን ጥንቃቄ ሊያደርግ ይገባልም ነው ያሉት።

አልፎ አልፎ ከምርመራ በኋላ አንዳንድ ሰዎች ውጤታቸውን ሳያውቁ ወደ ህብረተሰቡ ለመቀላቀል የሚሞክሩ መኖራቸውን በተደረገ ማጣራት ማረጋገጥ መቻሉንም አስረድተዋል።
ድርጊቱ ሃላፊነት የጎደለው ተግባር በመሆኑ ህብረተሰቡ ነቅቶ አካባቢውን እንዲጠብቅ ጥሪ ማቅረባቸውን ከሰላም ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

#FBC

የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.