Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያና እስራኤል በመረጃና ደህንነት  ዘርፍ  ተባብረው  ለመስራት  ተስማሙ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 26፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ኢትዮጵያና  እስራኤል  በመረጃና ደህንነት  ዘርፍ  ተባብረው  ለመሥራት  ስምምነት ላይ መድረሳቸውን  የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት  አስታውቋል ።

የእስራኤል ደህንነት ምክትል ሚኒስትር  ጋዲ ይቫርካን  ከብሄራዊ  መረጃና ደህንነት አገልግሎት ዳይሬክተር  ጄነራል ኮሚሽነር  ደምላሽ ገብረ ሚካኤል ጋር  ተገናኝተው  ውይይት አድርገዋል ።

በውይይታቸውም ሁለቱ አገራት  በአፍሪካ  ቀንድ ሽብርተኝነትን በጋራ ለመዋጋት፣ የመረጃ  ልውውጥ ለማድረግ ፣ በቴክኖሎጂ  ሽግግር እንዲሁም  በአቅም ግንባታ  ዘርፍ  ይበልጥ   ተባብረው ለመሥራት   መስማማታቸውን  ገልጸዋል ።

የብሄራዊ  መረጃና ደህንነት  አገልግሎት  ዳይሬክተር ጀኔራል ኮሚሽነር  ደምላሽ  ገብረሚካኤል በውይይቱ  ወቅት ÷  ኢትዮጵያና  እስራኤል  በመረጃና  ደህንነት ዘርፉ ተባብረው  ቢሰሩ  በአፍሪካ  ቀንድና አካባቢው  ሰላምና መራጋጋት በማጠናከር በኩል  ትልቅ አስተዋጽኦ  ሊያበረክቱ  ይችላሉ ብለዋል ።

የእስራኤል  ደህንነት  ምክትል ሚኒስትር ጋዲ  ይቫርካን በበኩላቸው÷ ኢትዮጵያ  በአፍሪካ  ቀንድ ቀጣና  ሰላምና መረጋጋት  በማስፈን  ረገድ  ትልቅ ሚና  ያላትና ተሰሚ  በመሆኗ  ምክንያት   እስራኤል  ከኢትዮጵያ  ጋር በመረጃና ደህንነት  ዘርፉ  ያላትን ትብብር  ይበልጥ ማጠናከር  እንደምትፈልግ  ገልጸዋል ።

ኢትዮጵያ  በመረጃ  ዘርፍ  የጀመረችውን  ለውጥ  እስራኤል   እንደምትደግፍም  ምክትል ሚኒስትር ጋዲ  ይቫርካን  ተናግረዋል ።

ኢትዮጵያና እስራኤልም በመረጃና ደህንነት ዘርፍ በጋራ  ለመሥራት  የደረሱትን  ስምምነት  በቅርቡ   ወደ ተግባር  ይሸጋገራል ተብሎ እንደሚጠበቅም  ብሄራዊ  መረጃና ደህንነት  አገልግሎት  የላከው  መረጃ አመልክቷል ።

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.