Fana: At a Speed of Life!

የኢንጅነር ስመኘው በቀለ የመታሰቢያ ሐውልት ተመረቀ

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 12 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ፕሮጀክት ስራ አስኪያጅ የነበሩት የኢንጅነር ስመኘው በቀለ የመታሰቢያ ሐውልት በዛሬው ዕለት ተመረቀ።

በምርቃት ሥነ ስርዓቱ ላይ የውሃ፣ መስኖና ኢነርጅ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጅነር ስለሺ በቀለ፣ የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጅ ሚኒስትር ዶክተር ኢንጅነር አብርሃም በላይ እና የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ህዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሄራዊ ምክር ቤት ጽህፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር ወይዘሮ ሮማን ገብረስላሴ ተገኝተዋል።

እንዲሁም የተለያዩ የመንግስት ስራ ሃላፊዎች፣ የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ሠራተኞች፣ የሃይማኖት አባቶች፣ የኢንጅነር ስመኘው ቤተሰቦችና ወዳጆች ተገኝተዋል።

በመታሰቢያ ሐውልቱ ምርቃት ሥነ ስርዓት በኦርቶዶክስ እምነት ስርዓት መሰረት የፍትሃትና የፀሎት ሥነ ስርዓት ተካሂዷል።

በተጨማሪም በሐውልቱ ምርቃት መርሃ ግብር ላይ የተገኙ የተለያዩ ድርጅቶች፣ ቤተሰቦችና ወዳጅ ዘመዶች የአበባ ጉንጉን ማስቀመጣቸውን ከኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

የቅዱስ ሲኖዶስ አባልና የምስራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ በበኩላቸው፥ ለሀገር አስተዋጽኦ ያደረጉ ሰዎች ቢያልፉም ስራቸው ግን ታሪክ ሆኖ ሁልጊዜ ሲታወስ እንደሚኖር ገልፀዋል።

የታላቁ ኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ሲታወስ ሁልጊዜም ኢንጅነር ስመኘው ለምልሞ ይኖራል ያሉት ብፁዕ አቡነ ዮሴፍ፥ እንደዚህ አይነት ሰዎች ለሚመጣው ትውልድ ህያው ሆነው እንደሚኖሩም አውስተዋል።

የሐውልት ምርቃቱ ከኢትዮጵያ የሰማዕታት መታሰቢያ 83ኛ ዓመት ጋር በታላቅ ድምቀት በመንበረ ፀባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል በታላቅ ሃይማኖታዊ ስነ ስርዓት ተከናውኗል።

ኢንጅነር ስመኘው በቀለ ሐምሌ 19 ቀን 2010 ዓ.ም ጠዋት በአዲስ አበባ መስቀል አደባባይ በተሽከርካሪያቸው ውስጥ ሞተው መገኘታቸው ይታወሳል።

ሐውልቱ በኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አማካኝነት የተሰራ ነው።

ትኩስ መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት የቴሌግራም ገፃችንን ሰብስክራይብ ያድርጉ!
https://t.me/fanatelevision

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.