Fana: At a Speed of Life!

በደቡብ ክልል ነገ ሕዝበ ውሳኔ እንደሚካሔድ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታወቀ

አዲስ አበባ፣ ጥር 28፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በደቡብ ብሔር፣ ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል ነገ ሕዝበ ውሳኔ እንደሚካሄድ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አስታውቋል፡፡

በክልሉ ስር በሚገኙ÷ የጋሞ፣ ጎፋ፣ ዎላይታ፣ ጌዴኦ፣ ኮንሶና፣ ደቡብ ኦሞ ዞኖች ሕዝበ ውሳኔ ይካሔዳል ብሏል ቦርዱ፡፡

በተጨማሪም በቡርጂ፣ ባስኬቶ፣ አሌ፣ አማሮ እና ደራሼ ልዩ ወረዳዎች ሕዝበ ውሳኔ እንደሚያካሂድ ነው ምርጫ ቦርድ ያስታወቀው፡፡

በሕዝበ ውሳኔው ላይ 5 ሺህ 274 የሀገር ውስጥ ታዛቢዎች ይሠማራሉ መባሉን ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

ቦርዱ በክልሉ ለሚካሄደው ሕዝበ ውሳኔ ባካሄደው የመራጮች ምዝገባ÷ 3 ሚሊየን 28 ሺህ 770 ሰዎች ድምፅ ለመስጠት መመዝገባቸውንም አሳውቋል፡፡

በድምፅ መስጫ ቀን አገልግሎት ላይ የሚውሉ ቁሳቁሶችን በሁሉም ምርጫ ጣቢያዎች ማሰራጨቱንም ነው ያረጋገጠው፡፡

የቁሳቁስ ስርጭቱ የተከናወነው በ31 ማዕከላት ስር ባሉ 3 ሺህ 771 ምርጫ ጣቢያዎች መሆኑ ተገልጿል፡፡

ጣቢያዎቹም ነገ ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽቱ 12 ሰዓት ክፍት እንደሚሆኑ ነው ቦርዱ ያስታወቀው፡፡

መራጮች በተጠቀሰው ሰዓት ወደተመዘገቡበት ጣቢያ በመሄድ ድምፃቸውን እንዲሰጡም አሳስቧል፡፡

 

 

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.