Fana: At a Speed of Life!

ፖሊስ ለህዳሴ ግድብ ጠንካራ የደጀን ኃይል መሆኑን በድጋሜ አረጋግጧል- ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል

አዲስ አበባ ፣ ግንቦት 19 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል ደመላሽ ገ/ሚካኤል ፖሊስ ለህዳሴ ግድባችን ጠንካራ የደጀን ኃይል መሆኑን በድጋሜ አረጋግጧል ሲሉ ገለጹ።
ኮሚሽነሩ ይህንን የገለጹት ዛሬ በወዳጅነት ፓርክ በተዘጋጀው የህዳሴው ግድብ ዋንጫ ርክክብ ፕሮግራም ላይ ተገኝተው መልዕክት ባስተላለፉበት ወቅት ነው።
ፖሊስ እጅግ የምንናፍቀውንና እንደ አይናችን ብሌን የምንከባከበውን የህዳሴ ግድባችንን የአካልና የገንዘብ መስዋትነት ጭምር በመክፈል በአስተማማኝ ሁኔታ (7/24) ሰዓታት በአይነቁራኛ ከውስጥና ከውጭ ፀረ ሰላም ሃይሎች ጥቃት እየጠበቀ ነው ብለዋል።
ለዘመናት የህዝባችን ምኞትና ቁጭት የሆነው የህዳሴው ግድብ በአሁኑ ወቅት ከ80 በመቶ በላይ በመጠናቀቁ በመጪው ወራትም ለ2ኛ ጊዜ የውሃ ሙሌት እንደሚደረግና ግድቡ እውን እንደሚሆን ይታወቃል ነው ያሉት።
ሆኖም የውጭ እና የውስጥ ጠላቶች የግድቡን ግንባታ ለማጨናገፍ፣ የሀገራችንን ሰላም ለማናጋትና ለማፍረስ የሀገር ውስጥ ተላላኪ ቅጥረኞችን በማስታጠቅና በፋይናንስ በመደገፍ አላማቸውን ለማሳካት የሞት ሽረት እያደረጉ እንዳሉ የሀገራችንና መላው የዓለም ሰላም ወዳድ ህዝብ ጭምር የሚያውቀው ሀቅ ነው ሲሉ ገልጸዋል።
ኮሚሽር ጀነራሉ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ከግድቡ መሰረት መጣል ጀምሮ ላለፉት 10 ዓመታት ከፍተኛ የሰው ሃይል በመመደብ ከሌሎች የፀጥታ ሃይሎች ጋር በመቀናጀት ግድቡን በመጠበቅ ላይ መሆኑን አብራርተዋል፡፡
በተለይም ባለፉት ሁለት አመታት ወደ ግድቡ በሚያስኬደው የተሸከርካሪ መንገድ ላይ የታጠቁ የፀረ ሰላምና ፀረ ልማት ሀይሎች ግንባታውን ለማደናቀፍና በግድቡ ውስጥ የሚሰሩ ሰራተኞችን ተረጋግተው እንዳይሰሩ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ቢያደርጉም በቦታው በተመደቡ የፖሊስ ሀይላችን ከፍተኛ መስዋትነት በመክፈል ህልማቸውን አጨናግፈዋል፣ ለዚህም መላው የሃገራችን የፖሊስ ሰራዊት ልትኮሩ ይገባል ብለዋል።
አያይዘውም የፌዴራል ፖሊስ በየደረጃው የሚገኝ አመራርና አባላት ለግድቡ ገንዘብ ማሰባሰብ ከተጀመረበት ጊዜ ጀምሮ ለሰባት ተከታታይ አመታት ያለማቋረጥ በቦንድ መልክ በስጦታ ከተሰጠው ውጪ ከደሞዛችን 205 ሚሊየን 429 ሺህ 542. ብር ያዋጣን ሲሆን ÷በአሁኑ ወቅትም ዋንጫው በተቋማችን ውስጥ በመዘዋወር ላይ ይገኛል ።
በመሆኑም በቀጣይ በየደረጃው የምንገኝ አመራርና አባላት የህዳሴው ግድብ ከፍፃሜ እስኪደርስ ድረስ በጉልበትና በገንዘብ እንዲሁም እስከ ህይወት መስዋትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆናችንን በኮሚሽኑ ማኔጅመንት ስም በድጋሚ እየገለጽኩ ÷ መላው የፌዴራል ፖሊስ አመራርና አባላት በመላው ሀገራችን የጀመርነውን የህግ የበላይነት ማስከበር ተልዕኮችንን አጠናክረን እንደምቀጥል አረጋግጣለሁ ብለዋል።
ግድቡ ይጠናቀቃል ኢትዮጵያችንም በድል ትሻገራለችም ብለዋል።
የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የወንጀል መከላከል ዘርፍ ሃላፊ ም/ኮሚሽነር ጀነራል መላኩ ፋንታ በበኩላቸው÷ የህዳሴ ግድብ ውስጥና ዙሪያው ተመድበው የነበሩት አመራሮችና አባሎች ግድቡ ሳይጠናቀቅ ወደ ሌላ የስራ ክፍል አንዛወርም በሚል ታላቅ ሀገራዊና ህዝባዊ ወኔ አንግበው ህዝቡና መንግስት የጣለባቸውን ተልዕኮ በመወጣት ላይ እያሉ የተለያዩ ተፈጥሮአዊ የጤና ችግሮች እንኳን ገጥሟቸው የግድቡን ፍፃሜ ሳናይ አንወጣም በሚል ለከፋ ጉዳት የተጋለጡበት ሁኔታ እንደነበረም ማስታወስ ይቻላል በማለት ተናግረዋል፡፡
የ ዶ/ር አረጋዊ በርሄ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ህዝባዊ ተሳትፎ አስተባባሪ ብሄራዊ ምክር ቤት ፅህፈት ቤት ዋና ዳይሬክተር በበኩላቸው ÷ፖሊስ ሰላምና ህግን ማስጠበቅ ብሎም ወንጀልን መከላከልና መመርመር ብቻ ሳይሆን በሀገሩ ልማት ተቆርቁሮ አስቦ ከልማት አርበኞች ጋር ተሰልፎ በዚህ ግንባርም ጀግንነቱን እያሳየ ስለሆነ ደስታና ክብር ይሰማኛል ማለታቸውን ከፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.