Fana: At a Speed of Life!

አሸባሪውን መንጋና ተላላኪዎቹን በጋራ ክንድ እንዋጋ!

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 21፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ)ወራሪው የሕወሓት የሽብር ቡድን ያለውን ኃይል ሁሉ አሰባስቦ ወደ ወሎ ግንባር የመጣበት ዋነኛ ዓላማ በግልጽ ይታወቃል።

ይህ መንጋ ዋና ዓላማው ከተማዋን ለመዝረፍ ብሎም ከመከላከያ ኃይላችን ከባድ መሣሪያን ለማግኘት ነበር።

መሥዋዕትነትን ለመክፈል ዝግጁ ሆኖ ጠንካራ ተጋድሎን እያደረገ የሚገኘው ጀግናው የመከላከያ ሠራዊታችንና መላው የጸጥታ ኃይላችን ይህንን የጠላትን ዓላማ ለማክሸፍ እየታገለ ነው።

ከሀገር ህልውና በላይ ምንም የለም ብሎ ስለሚያምን የጸጥታ ኃይሉ ከፍተኛ መሥዋዕትነትን እየከፈለ ይገኛል።

በመንጋ ያሰለፈው ኃይል ወደ መግደያ ወረዳው እየገባ ነው። ወደኋላ እንዳይመለስ ለእኩይ ዓላማው አሰልፎ ያስጨረሰው ትውልድ የት ገባ ለሚለው የሕዝቡ ጥያቄ መልስ መስጠት አይችልም። በመንገዱ ያለው ሕዝብም አያሳልፈውም።

አሸባሪው ሕወሐት ሕዝቡን ከመግደል፣ ከማዋረድና ከማንገላታት ባሻገር እጥፍተን እንጥፋ የሚል የሽብርተኛነት ዓላማውን ይዞ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል።

በወሎ በተለይም በደሴና አካባቢዋ አሁንም በቀጠለው ውጊያ ጠላት አለኝ የሚለውን ኃይል ከያለበት ጎትቶ እያሰለፈ ይገኛል።

ኢትዮጵያን የማፍረስ እኩይ ዓላማውን ለማሳካት በደሴ ከተማ ውስጥ ቀድሞ ባሰማራቸውና የሱን ሀገር የማፍረስ ዓላማ በሚደግፉ የሕወሓት ደጋፊ ባንዳዎችን በመጠቀም የጸጥታ ኃይላችንን ከፊትና ከኋላ ወግቷል።

በግንባር ከተደረገው ውጊያ ባለተናነሰ በከተማው ውስጥ ያሠማራቸው የሕወሓት ደጋፊ ባንዳዎች የሽብር ቡድኑን ዓላማ ለማሳካት ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል። ከሕዝቡ ጋር አብረው ለዘመናት መኖራቸውን ዋጋ አልሰጡትም።

በዚህም ምክንያት ሁሉም ዜጋ ተደራጅቶ በያለበት አካባቢውን በንቃት መጠበቅ ይኖርበታል። የጸጥታ ኃይሉን ከጀርባ የሚወጉትን የሕወሐት ደጋፊ ባንዳዎች ተከታተሎ ለሕግ ማቅረብም ተገቢ ነው።

በወረራ ይዞታ ሥር ላይ የምትገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎችም የሽብር ቡድኑን ለማስወገድ በሚደረገው የህልውና ትግል ተደራጅታችሁ አካባቢያችሁን ከዚህ የሽብር ቡድን ነጻ በማውጣት የበኩላችሁን ድርሻ እንድትወጡ ጥሪ ቀርቦላችኋል።

የተሳሳተ መረጃን በማኅበራዊ ገጾችም ሆነ በሌሎች ዘዴዎች እያሰራጩ የሚገኙና የሽብር ቡድኑ ዓላማ መጠቀሚያ የሆኑ ተቋማትና ግለሰቦችም ከዚህ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ መንግሥት ለመጨረሻ ጊዜ ያሳስባል።
በቀጣይም ሕጋዊ ርምጃ ይወስዳል።

መከላከያ ራሱን አደራጅቶና አጠናክሮ አስፈላጊውን መሥዋዕትነት እየከፈለ ነው። ሕዝቡም ራሱን የሠራዊቱ አካል አድርጎ አብሮ እንዲዋጋና መንጋውን እንዲቀብር መንግሥት ጥሪ ያቀርባል።

ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብም የሕወሐት የሽብር ቡድን እየፈጸመ የሚገኘውን ወረራ በማውገዝ፣ ወረራ ከተፈጸመባቸው የአማራና አፋር ክልል ሕዝቦች ጎን እንዲቆም መንግሥት ጥሪ ያቀርባል።
የኢትዮጵያ መንግሥት ሀገርን ከመበተን ለማዳን እያደረገ ያለውን ጥረት ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ መገንዘብ ይኖርበታል።

ዛሬም ለሀገሩ መሥዋዕትነትን እየከፈለ ሀገር የማዳን ተግባሩንም በጥንቃቄ እየተወጣ ለሚገኘው የመከላከያ ኃይላችንና ለመላው የጸጥታ መዋቅር ሁሉም ኅብረተሰብ ድጋፍ ማድረግ አለበት።

በሀገር ደረጃ ለተላለፈው የክተት ጥሪ ጠንካራ ምላሽን እየሰጠ የሚገኘው ኅብረተሰብም በሰው ኃይልም በደጀንነትም ያሳየውን ድጋፍ አጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል። ያለ መስዋዕትነት የሚገኝ ነፃነት የለምና!

የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.