Fana: At a Speed of Life!

በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን መልካ ጉባ አካባቢ በተካሄደ ዘመቻ አካባቢውን ከሸኔ ታጣቂ ቡድን ነፃ ማድረጉን የደቡብ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ አስታወቀ

አዲስ አበባ ፣ ሚያዝያ 20 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የደቡብ ዕዝ ጠቅላይ መምሪያ በኦሮሚያ ክልል ጉጂ ዞን በጉሚ ኤልዴሎ ወረዳ በመልካ ጉባ አካባቢ በተካሄደ ዘመቻ አካባቢውን ከሸኔ ታጣቂ ቡድን ነፃ ማድረጉን አስታወቀ፡፡
በዚህ ዘመቻ በአካባቢው ለአራት ዓመታት ያህል በሕዝቡ ላይ ስቃይ ሲያደርሱ ከነበሩ የቡድን ታጣቂዎች መካከል በርካታዎች መደምሰሳቸው ታውቋል።
የዕዙ የኋላ ደጀን አስተባባሪና የዘመቻው መሪ ኮለኔል ግርማ አየለ፥ በዚህ ውጊያ ከ200 በላይ የሸኔ ታጣቂዎች መገደላቸውን፣ ከ100 በላይ መቁሰላቸውንና 22 መማረካቸውን የገለፁ ሲሆን፥ ከተደመሠሡት ውስጥም የአሸባሪው ህወሓት ታጣቂዎች እንደሚገኙበት መናገራቸውን ከመከላከያ ሰራዊት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
መልካ ጉባ በተፈጥሮው በአስቸጋሪ የመሬት ገፅታና ከፍተኛ የውኃ ሙላት ባለው ዳዋ ወንዝ መከበቡ፣ ሸኔን የሚመሩ ከፍተኛ አመራሮች በአካባቢው መገኘታቸው፣ ታጣቂ ቡድኑ ለዓመታት በአካባቢው በመንቀሳቀስ ይዞታውን ማስፋቱ በዘመቻው ፈታኝ ሁኔታዎች እንደነበሩም አመላክተዋል፡፡
ሰራዊቱ ሁሉንም ችግሮች እንደአመጣጣቸው በመመከት ድል ማስመዝገብ ችሏልም ነው የተባለው፡፡
የዳዋ ወንዝ ከፍተኛ የውኃ ሙላትን እንደምሽግ በመጠቀም ለማጥቃት ሙከራ ያደረገውን የአሸባሪው ሸኔ ቡድንን ለመደምሰስ የሰራዊቱ ተነሳሽነት ከፍተኛ ነበር ያሉት ኮሎኔል ግርማ÷ ዘመቻው የህይወት መስዋዕትነት ያልተከፈለበትና በጥንቃቄ የተመራ እንደነበር አስረድተዋል፡፡
ሽብርተኛው ሸኔ በቦታው በርካታ ዜጎችን በመግደል በጅምላ እንደቀበረ ጠቅሰው÷ ሕዝቡ የዚህን አረመኔ ቡድን መጥፎ ተግባር በመረዳት ልጆቹን ከዚህ ሽብርተኛ ቡድን ጥሪ እንዲጠብቅና መከላከያ ኃይሉን እንዲያግዝ ጥሪ አቅርበዋል።
ሦስት ቀናትን በፈጀው ውጊያ ተማርከው እጃቸውን የሰጡ የሸኔ አባላት እንደገለጹት፥ የሸኔ ታጣቂ ቡድን በተለያዩ የማደናገሪያ ስልቶች በመጠቀም ወጣቱን እየመለመለ የቡድኑ መጠቀሚያ አድርጓል፡፡
ቡድኑ የኦሮሞን ሕዝብ ከመጨቆንና ከመግደል ያለፈ ምንም ፋይዳ የሌለው ስብስብ መሆኑን የተናገሩት ምርኮኞቹ÷ ወጣቶች የዚህ ሽብርተኛ ቡድን ዓላማ ተጋሪና ፈፃሚ እንዳይሆኑም መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን፡፡
You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.