Fana: At a Speed of Life!

የመስቀል በዓል ሃይማኖታዊ ትውፊቱን በጠበቀ መልኩ እንዲከበር ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ ቀረበ

 

 

አዲስ አበባ፣ መስከረም 13፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) የመስቀል በዓል ሃይማኖታዊ ትውፊቱን በጠበቀ መልኩ እንዲከበር ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ጥሪ አቅርባለች።

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዋና ሥራ አስኪያጅና የባህርዳር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አብረሃም÷ የደመራ እና መስቀል በዓል አከባበርን አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ አብረሃም በመግለጫቸው ÷በዓሉን ለማክበር የተዘጋጀን ክርስቲያኖች “ከመስቀሉ በቀር ሌላ ትምክህት ከኔ ይራቅ” የሚለውን በማሰብ ሊሆን እንደሚገባ አሳስበዋል።

 

ከመስቀሉ በቀር ሌላ ጉልበት፥ ሌላ ጥበብ ስለሌለን ቤተክርስቲያን በመስቀሉ ሰላምን ታውጃለች፤ ምዕምኑም ሰላምን እና ፍቅርን እየሰበከ ሊያከብረው ይገባል ብለዋል።

ምዕመኑ በዓሉን ሲያከብር ክርስቲያናዊ አለባበስን ጠብቆ ፥ ከመስቀሉ ጋር የማይሄዱ አልባሳትን እና ጥቅሶችን ከመያዝ በመቆጠብ እንዲሁም መንግሥት ላሰማራቸው የፀጥታ አካላት ተባባሪ በመሆን በዓሉን ሊያከብር እንደሚገባም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

 

ምዕመኑ የሌሎች ሃይማኖት ተከታዮች እና የፀጥታ አካላት ጋር በመተባበር ኢትዮጵያዊ ሥነ ምግባር በተላበሰ መልኩ በዓሉ በሰላምና በፍቅር እንዲከበር ቤተክርስቲያኗ ጥሪ አቅርባለች።

 

በቅድስት አባተ

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.