Fana: At a Speed of Life!

አቶ ሽመልስ አብዲሳ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ የሕዝቡ አጀንዳ ሆኖ እንደሚቀጥል አስታወቁ

አዲስ አበባ፣ ሚያዝያ 26፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ በ6ኛው ዙር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብርም የአመራሩና ሕዝባችን አጀንዳ ሆኖ ይቀጥላል ሲሉ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መሥተዳድር ሽመልስ አብዲሳ አስታወቁ፡፡

ወደራስ ለመመለስና ሁለገብ ብልጽግናን ለማረጋገጥ የተጀመረውን ጉዞ ለማሳካት የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃና እንክብካቤ በስፋት እየሠራን እንገኛለን ሲሉ አቶ ሽመልስ በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ገልጸዋል፡፡

በዚህ ዓመትም በ3 ነጥብ 2 ሚሊየን ሄክታር ላይ የተፈጥሮ ሀብት ጥበቃ ሥራ መካነወኑን ነው ያስታወቁት፡፡

ከዚህ ሥራ ጎን ለጎንም የኢኮ-ቱሪዝም መዳረሻ ቦታዎችን ዘላቂነትና ማራኪነት ለማረጋገጥ የተፋሰስና የአረንጓዴ ዐሻራ ልማት ሥራዎች በትኩረት እየተከናወኑ ነው ብለዋል፡፡

ለአብነትም በዳንዲ ሐይቅ ዙሪያ በአጠቃላይ 940 ሄክታር የሚሸፍኑ 10 ተፋሰሶች እንደሚገኙ ጠቁመው÷ ከዚህ ውስጥ 370 ሄክታር ላይ 45 ኪሎ ሜትር የአፈር እርከን፣ 32 ኪሎ ሜትር የድንጋይ እና የአፈር እርከን፣ 150 ኪሎ ሜትር የተራራ ሽፋን እርከን፣ 46 ኪሎ ሜትር ጥልቅ ቦይ እንዲሁም ውኃ አስራጊ 2 ሺህ 500 ማይክሮ ተፋሰሶች መሠራታቸውን አብራርተዋል፡፡

ይህ ንቅናቄ እየመጣ ባለው የ6ኛው ዙር የአረንጓዴ ዐሻራ መርሐ-ግብርም የአመራሩና የሕዝቡ አጀንዳ ሆኖ እንደሚቀጥል አስታውሰው÷ ለእስካሁኑ አፈጻጸምም ሕዝቡን አመስግነዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.