Fana: At a Speed of Life!

ኢትዮጵያ አሉ በተባሉ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ላይ አስፈላጊውን ማጣራት ታደርጋለች – ደመቀ መኮንን

አዲስ አበባ ፣ የካቲት 17 ፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ አሉ በተባሉ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ላይ አስፈላጊውን ማጣራት እንደምታደርግ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር እና ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን ገለጹ፡፡

አቶ ደመቀ መኮንን በ46ኛው የተመድ ሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ንግግር አድርገዋል፡፡

በንግግራቸውም ወሲባዊ ትንኮሳን ጨምሮ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች የመንግስት ትልቅ ትኩረት መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞም መንግስት አሉ በተባሉ ሰብአዊ መብት ጥቃቶች ላይ አስፈላጊውን ማጣራት በማድረግ ተሳትፈዋል የተባሉ አካላትን ተጠያቂ ለማድረግ ዝግጁ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

አቶ ደመቀ በንግግራቸው ኢትዮጵያ አሁን ላይ ገለልተኛ፣ ታማኝ እና ውጤታማ ሰብአዊ መብት ተቋም እንዳላትም አንስተዋል፡፡

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን የማይካድራውን ጭፍጨፋ ጨምሮ፥ በሰላማዊ ዜጎች ላይ የደረሱ ጉዳቶችን፣ ጾታዊ ትንኮሳ እና የሚስተዋሉ ከአያያዝ ጋር የሚስተዋሉ አድሏዊ አሰራሮችን የተመለከቱ ሰብአዊ ጉዳዮችን ሪፖርት ማድረጉንም አቶ ደመቀ ጠቁመዋል፡፡

መንግስት ከሰብአዊ መብት ጋር በተያያዘ የሚቀርቡ ግኝቶችን በአንክሮ እንደሚመለከታቸውና ኮሚሽኑ የሚያቀርባቸውን ምክረ ሃሳቦች በመተግበር የሰብአዊ መብት ሁኔታን ለማሻሻል ከኮሚሽኑ ጋር በቅርበት ለመስራት ያለውን ቁርጠኛ አቋምም አስረድተዋል፡፡

በትግራይ ክልል እየተካሄደ ካለው ሰብአዊ ድጋፍ ጋር በተያያዘ ባደረጉት ንግግር፥ መንግስት ከሃገር ውስጥና ዓለም አቀፍ አጋር አካላት ጋር በመሆን በክልሉ ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ዜጎች አስፈላጊውን ሰብአዊ ድጋፍ እያደረገ መሆኑንም አስረድተዋል፡፡

ከዚህ ጋር ተያይዞም 92 የምግብ ማሰራጫ ማዕከላት ተቋቁመው ድጋፍ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች ሰብአዊ ድጋፍ እየተሰራጨ መሆኑንም አስታውቀዋል፡፡

በንግግራቸው በውጭው ዓለም በሚገኙ የህወሓት ደጋፊዎችና አንዳንድ የሚዲያ አካላት የሚነዛው ፕሮፓጋንዳና የሃሰት መረጃ መሬት ላይ ያለውን እውነታ ያላገናዘበ መሆኑንም ነው የገለጹት፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.