Fana: At a Speed of Life!

የሩሲያ ባለሃብቶች በኢትዮጵያ በማዳበሪያና ብረታብረት ዘርፎች መሰማራት እንደሚፈልጉ ገለጹ

አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 29፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በሩሲያና በኢትዮጵያ የግል ባለሃብቶች ሊመሰረቱ የሚችሉ የጋራ የኢንቨስትመንት እድሎችን መሰረት ያደረገ ምክክር በሞስኮ ተካሂዷል፡፡

በመድረኩ የአምራች ኢንዱስትሪው በኢኮኖሚ ግንባታ ውስጥ ሊኖረው የሚገባውን ጉልህ ሚና ይበልጥ ለማጠናከር በማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ኢንቨስት ከሚያደርጉ የውጭ ባለሃብቶች የዕውቀትና የቴክኖሎጂ ልምድ መቅሰም መቻሉ ተጠቁሟል፡፡

የውጭ ቀጥተኛ ኢንቨስትመንት መሳብ ፣ የጋራ ኢንቨሰትመንት በብዛት ማስገባትና ቀጣይነት ያለው ስራ መስራት አስፈላጊ ስለመሆኑ ልምድ መወሰዱንም በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የብቃትና ፈቃድ አገልግሎት መሪ ሥራ አስፈፃሚ ካሳዬ ዋሴ ተናግረዋል፡፡

የኢትዮጵያና ሩሲያ የዲፕሎማሲ ግንኙነት በትምህርት፣ በሳይንስና ቴክኖሎጂ ረጅም ጊዜ አስቆጥሯል ያሉት ስራ አስፈፃሚዋ÷ በንግድና ኢንቨስትመንት የተጀመረውን ማስቀጠል እንደሚገባም ገልጸዋል፡፡

ሩሲያ ለአፍሪካ ገበያ ትኩረት እየሰጠች ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የሀገሪቱ ባለሃብቶች ኢትዮጵያን ቀዳሚ ተመራጭ እያደረጉ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

የሩሲያ ባለሃብቶች በከባድ ኢንዱስትሪዎች ማለትም በማዳበሪያ፣ በኬሚካል፣ በብረታብረትና በከበሩ ማእድናት ዘርፎች ላይ መሰማራት እንደሚፈልጉ አንስተዋል፡፡

በተጨማሪም በአበባ፣ በግብርና ማሽነሪ፣ በሕክምና መሳሪያዎችና ክትባት እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች የመሰማራት ፈላጎት ማሳየታቸውን ገልፀዋል፡፡

በጨርቃ ጨርቅ፣ በብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ እንዲሁም በፋርማሲዩቲካል ዘርፎች በጋራ ለመስራት ከ6 ድርጅቶች ጋር ቅድመ መግባባት ላይ መደረሱንም ጠቁመዋል፡፡

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.