Fana: At a Speed of Life!

ከ600 ሺህ የሚበልጡ ዘመናዊ ቀፎዎችን ለአርሶ አደሩ ማድረስ ተችሏል – አቶ ሽመልስ አብዲሳ

አዲስ አበባ፣ መጋቢት 5፣ 2016(ኤፍ ቢ ሲ) በበጀት ዓመቱ እስካሁን ከ600 ሺህ የሚበልጡ ዘመናዊ ቀፎዎችን ለአርሶ እና አርብቶ አደሩ ማድረስ እንደተቻለ የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ሽመልስ አብዲሳ ገለጹ፡፡

አቶ ሽመልስ አብዲሳ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው÷ የለውጡ መንግስት ዓላማ የበለፀገች ሀገር እውን ማድረግ ነው ብለዋል፡፡

ግቡን ለማሳካትም በዓለም አቀፋዊነት እና ተወዳዳሪነት የሃሳብ ማዕቀፍ የተቃኘ የኢኮኖሚያዊ እይታን የሚከተል ይሆናል ሲሉም ነው የገለጹት፡፡

በዚህም በግብርናው ዘርፍ፣ የግብርና ሥነ-ምህዳር አቅምን ከግምት ያስገቡ 27 የሚሆኑ ኢኒሼቲቮች በመተግበር ላይ ይገኛሉም ብለዋል።

ከእነዚህ መካከል በ2013 ዓ.ም በጅማ ከተማ የታወጀው “የጅማ አዋጅ” አንዱ መሆኑን ጠቅሰው ÷ አዋጁ “ኦሮሚያን የማር ባህር እናደርጋለን” በሚል መሪ ሃሳብ የተያዘ የማር ልማት ኢኒሼቲቭ ነበር ነው ያሉት፡፡

ኢኒሼቲቩ ዘመናዊ ቀፎና ሳይንሳዊ የማነብ እውቀት ማስፋፋትን ያለመ ሲሆን ÷ እስካሁን በ15 ዞኖች ውስጥ በሚገኙ 175 ወረዳዎች ማስፋፋት መቻሉንም ነው የተናገሩት፡፡

በ2015 ዓ/ም፣ 345 ሺህ ዘመናዊ ቀፎዎችን ለአርሶ እና አርብቶ አደሮች በማቅረብ 86 ሺህ ቶን ማር ማምረት ተችሎ እንደነበርም አስታውሰዋል፡፡

በዚህ ዓመትም 1 ሚሊየን ዘመናዊ ቀፎዎችን 200 ሺህ ለሚበልጡ አርሶ/አርብቶ አደሮች በማከፋፈል 114 ሺህ ቶን ማር እና 7 ሺህ ቶን ሰም ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑንም ነው ያመላከቱት፡፡

በእስካሁኑ አፈፃፀም ከ600 ሺህ የሚበልጡ ዘመናዊ ቀፎዎችን ለአርሶ/አርብቶ አደሩ ማድረስ የተቻለ ሲሆን ፥ በቀሪው ጊዜም የዓመቱን እቅድ ተግባራዊ ለማድረግ በትኩረት እንደሚሰራ ጠቅሰዋል፡፡

ከመነሻው እንደታሰበው ፥ ዓለም አቀፋዊነትና ተወዳዳሪነት በሚሉ የሃሳብ ማዕቀፎች የተቃኘው የማር ልማት ኢኒሼቲቭ፣ ክልሉ ለውጭ ገበያ የሚያቀርባቸውን ምርቶች ብዝሃነትና መጠን በማሳደግ ላይ ይገኛልም ነው ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፡፡

 

 

You might also like

Leave A Reply

Your email address will not be published.